አባታቸው ይስሐቅ ሙሴ የየመን ተወላጅ ይሁዲ ናቸው። መጽሐፍ ቅዱስን በዕብራይስጥ የዘለቁ ሲሆኑ፤ የወርቅና ብር አንጥረኛ ባለ እጅ ነበሩ።
እናታቸው የገጠር የቤት እመቤት የነበሩ ናቸው። በባለቤታቸው ይስሐቅ ሙሴ አማካኝነት መጽሐፍ ቅዱስን በኦሮምኛ ተምረዋል።
የፕሮፌሰር ኤፍሬም ዕትብት ነጆ-ወለጋ ቢቀበርም፤ ዘመናዊ ትምህርት አማልሏቸው ወደ አገረ አሜሪካ ዘልቀው እስካሁኑ የአረጋዊ ዕድሜያቸው ድረስ እዚያው ከትመው አሉ። የታላቁ መጽሐፍ ይትባሃል ‘ነብር ዝንጉርጉርነቱን፤ ኢትዮጵያዊ ማንነቱን ሊለውጥ ይችላልን?’ እንዲል፤ “እኔ መጀመሪያም፤ መጨረሻም ኢትዮጵያዊ ነኝ” ይላሉ።

የፋሺስት ኢጣልያ ጠብመንጃ አረሮችና የቦምብ ፍንዳታዎች በለጋ ዕድሜያቸው ሕይወት ሲቀጥፉ በማየታቸው ጦርነት ጠል፤ ሰላም ወዳድ እንዲሆኑ ስነ ልቦናዊ ተጽዕኖ ያሳደረባቸው መሆኑን ያወጋሉ።
በትምህርቱ ዘርፍ፤ ባይዘልቁበትም የሕክምናውን ደጅ ረግጠዋል። በሙዚቃው መስክ ጅማሯቸውን ዳር ባያደርሱትም በሥነ ጥበቡ ዓለም ግማሽ መንገድ ገፍተው መጓዛቸው ግና እውነት ነው። ክህሎታቸውም ከኢትዮጵያው የመጨረሻው ንጉሠ ነገሥት ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዘንድ አቅርቦ ሞገስ አላብሷቸዋል።

ለሊህቅነት መታወቂያቸው የሆነው ግና የአባታቸው በጎ ተጽዕኖ ውርሰ አሻራ ገዝፎ የሚታይበት የሃይማኖቱ መስክ ነው። PhD አግኝተው ተጠበውበታል። ፕሮፌሰር ተብለው ካባ ደርበውበታል።
የክፍል አንድ ግለ ታሪክ ትረካቸው የሚዳስሰውም ይህንኑ ነው።

