ግራ ክንፈኛው ሉላ ዳ ሲልቫ የቀኝ አክራሪ ተቀናቃኛቸውን የወቅቱን ፕሬዚደንት ጃይር ቦልሶናሮን ድል ነስተው የብራዚል ፕሬዚደንታዊ ምርጫ አሸናፊ ሆኑ።
የፕሬዚደንታዊ ምርጫ ድሉ በ2018 ዘብጥያ ለ19 ወራት ተጥለው ለነበሩት ሉላ አስደናቂ ውጤት ተብሏል።
ሉላ ለእሥር ተዳርገው የነበሩት በሙስና ተወንጅለው የነበረ ቢሆንም በጠቅላይ ፍርድ ቤት ውሳኔ ባለፈው ዓመት ነፃ ወጥተዋል።
ዳ ሲልቫ ቀደም ሲል ከ2003-2010 ብራዚልን በፕሬዚደንትነት መርተዋል።
የፕሬዚደንታዊው ምርጫ ውጤት ብራዚል ውስጥ ባለፉት አሠርት ዓመታት ታይቶ የማይታወቅ ፅንፈኛ ቀኝ አክራሪ ተብሎ ሲተች የነበረውን መንግሥት ለክስመት ዳርጓል።
ሶማሊያ
ሞቃዲሾን የናጠው የመኪና ላይ የተጠመደ ቦምብ ጥቃት ከ100 በላይ ሕይወቶችን ቀጥፏል።
የአካባቢው ፖሊስ እንዳመለከተው አንደኛው ጥቃት ያነጣጠረው በትምህርት ሚኒስቴር ላይ ሲሆን፤ የተቀሩት ሁለቱ የመንግሥት ቢሮዎች፣ ሆቴሎችና ምግብ ቤቶች ላይ ነው።

እስካሁን ጥቃቱን አስመልክቶ ኃላፊነቱን የወሰደ ቡድን አልተደመጠም።

