በኢትዮጵያ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶችን ተጠያቂነት ለማረጋገጥ መሰረታዊ የሽግግር ፍትሕ ፖሊሲን ለማዘጋጀት፤ ግብዓት ማሰባሰቢያና ምክክር መርሐ ግብር ማስጀመሪያ መድረክ ተካሂዷል።
በመድረኩ ከፍተኛ የፌዴራልና የክልል የመንግስት የስራ ኃላፊዎች፣ ዲፕሎማቶች፣ የፖለቲካ ፓርቲ አባላት፣ የሰብዓዊ መብት ተቆርቋሪዎችና ሌሎች የሕብረተሰብ ክፍል ተወካዮች ተገኝተዋል።
በሽግግር ፍትሕ ሂደት እና አስፈላጊነት ዙሪያ ጥናታዊ ፅሁፎች ቀርበው ውይይት ተደርጎባቸዋል።
መሰረታዊ የሽግግር ፍትህ በኢትዮጵያ እስከ ዛሬ የተፈጸሙ ጉልህ በደሎችን እውቅና መስጠት፣ ለበደሎች ተጠያቂነት ማስፈንና ተጎጂዎችን መካስ እና ሌሎች ተመሳሳይ ሰብዓዊ መብት ጥሰት እንዳይፈፀም እንደሚያስችል በጥናቶቹ ተመላክቷል።
የሽግግር ፍትህ በየጊዜው የተፈጸሙ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች እና ቁርሾዎች አግባብነት ባለው፣ የተቀናጀና አሳታፊ በሆነ መልኩ እንዲፈቱ፤ ዲሞክራሲ ሸግግር ሂደት እና ዘላቂ ሰላም ለማረጋገጥ ወሳኝ መሆኑ ተገልጿል፡፡
ፖሊሲው በዋናነት በኢትዮጵያ የተፈጸሙ ጉልህ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች፣ በደሎችና ቁርሾዎችን እውነትን፣ ፍትሕን፡ ሰላም እና እርቅን መሰረት ባደረገ መልኩ በሽግግር ፍትህ ስልት እንዲፈቱ ማስቻል ነው ተብሏል።
የፍትሕ ሚኒስትር ዶክተር ጌዴዎን ጤሞቲዎስ እንዳሉት፤ ባለፉት አራት ዓመታት በፌዴራል ደረጃ ብቻ ከ10 ሺህ በላይ ግለሰቦች "በማንነት ተኮር ግጭት" በቁጥጥር ስር ውለው ክስ እንደተመሰረተባቸው ተናግረዋል።
"የተጠርጣሪዎችና ተጎጂዎች ብዛት በተለመደው አሰራር ብቻ ማስተናገድ እንደማይቻል እና በኢትዮጵያ አሁናዊ ዐውድ የሽግግር ፍትህ እንደሚያስፈልጋት ማሳያ ነው " ብለዋል።
የሽግግር ፍትሕ ፖሊሲ አቅጣጫዎች ላይ ለቀጣይ ሶስት ወራት በ59 ቦታዎች ውይይቶችን በማድረግና ግብዓት በማሰባሰብ በ2016 ዓ.ም መጀመሪያ ላይ ፖሊሲው ተጠናቆ ወደ ትግበራ እንደሚገባ ገልጸዋል።
ፖሊሲው የሚዘጋጀው በሕገ መንግስቱ እና ኢትዮጵያ በፈረመቻቸው ዓለም አቀፍ ድንጋጌዎች ወሰን ውስጥ እንደሆነም ነው የተናገሩት።
የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን ኮሚሽነር ዶክተር ዳንኤል በቀለ በበኩላቸው፤ የሽግግር ፍትህ ትግበራ ዐውድ ተኮር መሆን እንዳለበት ገልጸዋል።
መንግስት በኢትዮጵያ የተፈጸሙ መልከ ብዙ ሰብዓዊ መብት ጥሰቶችን ተጠያቂነት ለማረጋገጥ "የሽግግር ፍትሕ አማራጭን ለመተግበር መሞከሩ ትልቅ እምርታ ነው" ብለዋል፡፡
የመድረኩ ተሳታፊዎችም በበኩላቸው አካታች፣ ተጎጂዎችን ማዕከል ያደረገ፣ ዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብቶች ድንጋጌዎችን ያከበረ የሽግግር ፍትሕ ሂደትን መተግበር እንደሚያስፈልግ ገልጸዋል።
ያለፉ ችግሮችን በጋራ በመፍታት የወደፊቷን ኢትዮጵያ በትብብር መገንባት እንድሚገባ ተናግረዋል።
የሽግግር ፍትሕ ፖሊሲው በመሰረታዊነት ውጤታማ እንዲሆን የኢትዮጵያን ዐውድ መሰረት ያደረገና ሁሉንም የሕብረተሰብ ክፍል አሳታፊ መሆን አለበት ብለዋል ሲል ኢዜአ ዘግቧል።