የመብቶችና ዴሞክራሲ ዕድገት ማዕከል (ካድር) በኤሊያና ሆቴል ባዘጋጀው ፌስቲቫል በዓለም አቀፍ ደረጃ የሚታሰበውን የሰብዓዊ መብቶች ቀንን አከብሯል።
ማዕከሉ ፌስቲቫሉን ሲያከብር በመሠረታዊ የሰብዓዊ መብቶች ላይ ያሰለጠናቸውን 370 የሁለተኛ ደረጃ ተማሪዎች በማስመረቅ ሲሆን፣ በኢትዮጵያ በሰብዓዊ መብቶችና ተያያዥ መብቶች ላይ የሚሠሩ ድርጅቶችም ሥራቸውን በተዘጋጀው የጎን ዐውደ ርዕይ አቅርበዋል፡፡
የመብቶችና ዴሞክራሲ ዕድገት ማዕከል ለተከታታይ ሳምንታት በአዲስ አበባና በስድስት የክልል ከተሞች ሲሰጣቸው የነበሩ መሠረታዊ የሰብዓዊ መብቶች ሥልጠናዎችን ሲከታተሉ የነበሩ ተማሪዎች በፌስቲቫሉ ላይ የታደሙ ሲሆን፣ ከተማሪዎቹ መካከልም በውጤት ተለይተው የጥያቄና መልስ ውድድር አድርገዋል፡፡

Human Rights Activists. Credit: CARD
ሠልጣኞቹ በአዲስ አበባ፣ አዳማ፣ ደብረ ብርሃን፣ ሐዋሳ፣ ሐረር፣ ድሬ ዳዋ እና ቢሾፍቱ በተለያዩ የግልና የመንግሥት ትምህርት ቤቶች የሚማሩ የሁለተኛ ደረጃ ተማሪዎች ሲሆኑ፣ በመሠረታዊ የሰብዓዊ መብቶች፣ በሥርዓተ ፆታ እኩልነት፣ በመደራጀት መብቶች፣ በመሰብሰብ መብቶች እና ሰላማዊ ሰልፍ በማድረግ መብቶች ላይ ሥልጠናዎችን ወስደዋል፡፡
ፌስቲቫሉን አስመልከቶ የካርድ ዋና ዳይሬክተር በፍቃዱ ኃይሉ ባስተላለፉት መልዕክት፣ “በረዥም ዓመታት የኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ ሰብዓዊ መብቶችን የሚያከብር ዴሞክራሲያዊ ስርዓተ ማኅበር የመገንባቱ ሒደት እስካሁን አልተሳካም። በየጊዜው የሚከሰቱ የፖለቲካ ለውጦች ለሰብዓዊ መብቶች መከበር ያላቸው ቁርጠኝነት እምብዛም ዘላቂ ሲሆኑ አይስተዋልም። ለሰብዓዊ መብቶች የሚታገሉ ተቋማት እና ግለሰቦች ቁጥርም ከሕዝብ ብዛታችን አንፃር ዝቅተኛ ነው። በዚህም ምክንያት ከተፈጥሯዊ የሰው ልጅ ነፃነት እና ክብር የሚቀዱትን ሰብዓዊ መብቶችን የኢትዮጵያ መንግሥት እንዲያከብር፣ እንዲያስከብር፣ እና ለሰብዓዊ መብቶች መከበር ሁኔታዎችን እንዲያሟላ የሚያደርግ ሕዝባዊ/ትውልዳዊ መሠረት አልተጣለም ማለት ይቻላል፤” ሲሉ ተናግረዋል፡፡

Befekadu Hailu, Director of Center for Advancement of Rights and Democracy - CARD. Credit: CARD

Dr Daniel Bekele, Chief Commissioner of the Ethiopian Human Rights Commission (EHRC). Credit: EDUARDO SOTERAS/AFP via Getty Images
የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን ኮሚሽነር ዳንኤል በቀለ (ዶ/ር) በፌስቲቫሉ መፅሔት ላይ ባስተላለፉት መልዕክት፣ “የሰብዓዊ መብቶች ባሕል ማለት አንድም ባለመብቱ (right-holder) ያለ ስጋትና ፍርሃት፣ እንዲሁም ያለ አስታዋሽና ያለ ግርታ መብቱን የመጠየቅ እና የሚጠይቀውን መብት ግዴታ ፈጻሚ አካል (duty-bearer) የሚያውቅበት ሁኔታ መፈጠርን ያመላክታል፤” ያሉ ሲሆን፣ ይህንን አመለካከትና አስተሳሰብ ለመፍጠር ገና ብዙ ይቀረናል ብለዋል፡፡
ኮሚሽነሩ አክለውም “አዲሱ የሀገራችን ትውልድ የሰብዓዊነት መንገድ በጽኑ ፍላጎት እንዲመርጥ ፋና እና ምሳሌ የሚሆኑ ሰዎችንና መልካም ተሞክሮዎች ማሳየትና መምራት የእኔም ሆነ የባልደረቦቼ እንዲሁም በሰብዓዊ መብቶች ሥራ ውስጥ የተሰማሩ ባለሞያዎች ሁሉ ከፍተኛ ጥረት ልናደርግበት የሚገባ ኃላፊነት ነው። ወጣቶችና ታዳጊዎችም “ሰብዓዊ መብቶች ባሕል የሆኑባት ኢትዮጵያን ማየት” የሚለው ራዕያችን የእናንተን የዛሬ አቅምና የነገ ሕይወታችሁን የሚያልም መሆኑን አውቃችሁ፤ ዛሬ በገጠመን ችግሮች ሳትሸነፉ ሰብዓዊ መብቶችን ባሕል የማድረግ የበኩላችሁን ኃላፊነት እንድትወጡ አደራ እላለሁ፤” ሲሉ አሳስበዋል፡፡
የአዲስ የሰብዓዊ መብቶች ተሟጋቾች ትውልድ ተከታታይ ሥልጠና በ2013 እና 2014 የትምህርት ዓመታት የተጀመረ ሲሆን፣ በመጀመሪያው ዙር ተከታታይ ሥልጠና 364 በአዲስ አበባ የሚገኙ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተማሪዎች ሥልጠናውን እንዲያገኙ የተደረገ ሲሆን፣ ከመጀመሪያው ዙር ሠልጣኞቻችን መካከል በየትምህርት ቤቶቻቸው የሰብዓዊ መብቶች ግንዛቤ ማሳደጊያ ንቅናቄዎችን የጀመሩ እንደሚገኙበትም ተገልጿል።
ሥልጠናውን በ2015ም በመቀጠል ተዳራሽነታችንን በማስፋት በአዲስ አበባ እና በክልል ከተሞች 370 የሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ተማሪዎችን ማሠልጠን መቻሉን ካርድ ገልጿል፡፡
[ ደመቀ ከበደ ፡ አዲስ አበባ]