አውስትራሊያ፣ ዴንማርክ፣ ጀርመን፣ ኔዘርላንድስ፣ እንግሊዝና ዩናይትድ ስቴትስ በሰሜን ኢትዮጵያ በመካሔድ ላይ ያለው ግጭትና ሰብዓዊ ቀውስ በእጅጉ ያሳሰባቸው መሆኑን ኦክቶበር 12 ቀን 2022 / ጥቅምት 2 ቀን 2015 በጋራ ባወጡት መግለጫ ገለጡ።
አገራቱ በጋራ መግለጫቸው የኢትዮጵያ መንግሥትና የትግራይ ክልል አስተዳደር ወታደራዊ ጥቃቶችን በአስቸኳይ እንዲገቱ፣ ከተኩስ አቁም ስምምነት ላይ እንዲደርሱ፣ ገደብ ያልተጣለበት፣ ዘላቂ የረድዔት ተደራሽነት እንዲኖርና በአፍሪካ ኅብረት መሪነት በሚካሔድ የሰላም ንግግር አማካይነት ተደራድረው ከስምምነት ላይ እንዲደርሱ ሲሉም አሳስበዋል።
አክለውም፤ በሰሜን ኢትዮጵያ እየጨመረ የመጣውን የኤርትራ ወታደራዊ ኃይል ተሳታፊነት እናወግዛለን፣ የኤርትራ ጦር በሰሜን ኢትዮጵያ እያካሔደ ያለውን ዘመቻ ገትቶ እንዲወጣና ማናቸውም ግጭት አባባሽ የውጭ ተዋናዮች በሙሉ ከድርጊቶቻቸው እንዲታቀቡ ጥሪ እናቀርባለን ብለዋል።
የጋራ መግለጫው፤ በኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽንና በተመድ በኢትዮጵያ ጉዳይ ዓለም አቀፍ የሰብ ዓዊ መብቶች ተጠባቢዎች ኮሚሽን ሪፖርቶችን አካትቶ በርካታ ሪፖርቶች በኢትዮጵያና ኤርትራ ወታደሮች፣ በትግራይ ጦሮች፣ እንደ ፋኖ ያሉ ታጣቂ ተዋናዮች ግጭቱ በኖቬምበር 2020 ከተቀሰቀሰ አንስቶ ሕገ ወጥ ግድያዎች፣ አካላዊና ፆታ ተኮር ጥቃቶች መፈፀማቸውን እንደሚያመልክቱ በመጥቀስ፤ የግጭቱ መቀጠልም ተጨማሪ የሰብዓዊ መብቶች ጥሰቶችን እንደሚያባብስ አሳስቧል።
ስድስቱ አገራት ማናቸውንም ዓይነት በሰላማዊ ሰዎች ላይ የሚፈፀሙ የአመፅ ተግባራትን እንደሚያወግዙ አስታውቀዋል። ሁሉም ተፋላሚ ኃይላት ግጭትን መፍቻ ወታደራዊ መፍትሔ እንደሌለ ልብ እንዲሉና የኢትዮጵያ መንግሥትና የትግራይ ክልል አስተዳደር ዘላቂ ሰላምን ለኢትዮጵያ ማስገኘት ትልሙ ባደረገው የአፍሪካ ኅብረት መራሽ የሰላም ንግግር ላይ እንዲሳተፉ ጥሪያቸውን አቅርበዋል።
ማናቸውም ዘላቂ መፍትሔ ለሰብዓዊ መብቶች ጥሰቶች ተጠያቂነት እንዲኖር የሚያካትት መሆን እንዳለበትም አሳስበዋል።
ይህንኑ የስድስቱን አገራት መግለጫ ተከትሎ በኢትዮጵያና ኤርትራ መንግሥትታ በኩል ይፋዊ ምላሽ ለጊዜው ባይሰጥም፤ የኤርትራ የኢንፎርሜሽን ሚኒስትር የማነ ገብረመስቀል በቲዊተር ገፃቸው ምንም እንኳ 'ለሉላዊ ሰላምና ፀጥታ የሚያስከትላቸው መዘዞች ብርቱ ቢሆንም በተወሰኑ ሪጂኖች ጦርነትና ግጭትን የሚያባብሱ ሆነው ሳለ፤ ራስን ለመከላከል የሚደረጉ ተግባራትን ግና ያወግዛሉ' በማለት ነቀፌታን ሰንዝረዋል።