መንግስት የስራ አስፈጻሚ አባሉን ጋዜጠኛ ዳዊት በጋሻውን ጨምሮ “ያለምንም የህግ አግባብ” ያሰራቸውን የመገናኛ ብዙኃን ባለሙያዎችን “በአስቸኳይ እንዲፈታ” የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ባለሙያዎች ማህበር ጠየቀ
የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ባለሙያዎች ማህበር መንግስት የመገናኛ ብዙኃን ባለሙያዎችን እስር እና እንግልት እንዲያቆም ዛሬ ሚያዝያ 06 ቀን 2015 ዓ/ም ባወጣው መግለጫ ጠይቋል።
ማህበሩ በኢትዮጵያ እየተካሄደ ያለውን የመገናኛ ብዙኃን ባለሙያዎችን እስር እና እንግልት አስመልክቶ እንዳለው የመገናኛ ብዙኃን ባለሙያዎች ወገንተኝነታቸው ለህዝብና ለእውነት መሆኑን አስታውሷል።
ሆኖም ባለሙያዎቹ በሥራቸው ላይ ስህተት በሚሰሩበት ወቅት በሕግ አግባብ መጠየቅ እንዳለባቸው እና የሕግ የበላይነት መከበር እንዳለበት በፅኑ እንደሚያምንም ጨምሮ ገልጿል።
ይሁን እንጅ "ከለውጡ በኋላ" በኢትዮጵያ የመገናኛ ብዙኃን ነፃነት እንዲረጋገጥ ብዙ ተስፋ አድርጎ እንደነበር የገለጸው ማሕበሩ፤ ቢሆንም ከጊዜ ወደ ጊዜ ባለሙያዎች የሚሰሩበት አውድ እየጠበበ ጋዜጠኞች ሥራቸውን በነፃነት እንዳይሰሩ በመንግስት የፀጥታ አካላት እየተሸማቀቁ እና እንግልት እየደረሰባቸው እንደሆነ መታዘቡን አስታውቋል።
በዚህም፤ የመገናኛ ብዙኃን ባለሙያዎች ማህበር መስራችና የሥራ አስፈፃሚ አባል እንዲሁም የማህበሩ የህዝብ ግንኙነት ክፍል ኃላፊ ጋዜጠኛ ዳዊት በጋሻውን ጨምሮ አራጋው ሲሳይ፣ ገነት አስማማው፣ ጌትነት አሻግሬ፣ በየነ ወልዴና ቴዎድሮስ አስፋው በመንግሥት ሃይሎች በቁጥጥር ሥር መዋላቸውን ገልጿል።

Credit: EMMPA
በመንግሥት ሃይሎች በቁጥጥር ሥር ከዋሉት የመገናኛ ብዙኃን ባለሙያዎች ውስጥ አንዳንዶቹ ያሉበት ቦታ እና ምን ሁኔታ ላይ እንዳሉ እንኳን ቤተሰቦቻቸውም በቂ መረጃ ሳይኖራቸው በእስር ላይ እንደሚገኙም የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ባለሙያዎች ማህበር አስታውቋል።
ማህበሩ በመግለጫው "ጋዜጠኞች ያለ ፍርድ ቤት ማዘዣ እየታሰሩ፣ እየታፈኑና ቤታቸውና ቢሯቸው እየተበረበረ መሆኑ ባለሞያዎች ሥራቸውን በነፃነት እንዳይሰሩ፤ የፕረስ ምህዳሩ የበለጠ እንዲጠብ እያደረገ ነው" ያለ ሲሆን ማህበሩ የተቋቋመውም እንደዚህ አይነት ሙያውን የሚያቀጭጩ ጫናዎችን ለመታገል በመሆኑ እርምጃዎቹን በፅኑ እንደሚያወግዝ አስታውቋል።
ጋዜጠኞች በወንጀል ሲጠረጠሩ ጉዳያቸውን እስር ቤት ሳይቆዩ መከታተል እንደሚችሉ ከኹለት ዓመት በፊት በወጣው በመገናኛ ብዙኃን አዋጅ ቢደነገግም ተግባራዊ አለመደረጉ እንደሚያሳስበውም ገልጿል፡፡
በዚህም መሠረት፤ "መንግሥት የፕረስ ነፃነት እንዲረጋገጥ ያጸደቃቸውን ህገ-መንግስታዊና ዓለም አቀፋዊ ህጎች እንዲያከብርና ውስጡን እንዲፈትሽ" የጠየቀው ማህበሩ በተጨማሪም ያለምንም የህግ አግባብ ያሰራቸውን
የመገናኛ ብዙኃን ባለሙያዎች በአስቸኳይ እንዲፈታ እና ባለሙያዎች ላይ የሚያደርሰውን ማሸማቀቅ እንዲያቆም ጠይቋል።
በተጨማሪም ልዩ ልዩ የመገናኛ ብዙኃን ባለሙያዎች ማህበራትና የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶች የማህበሩ አጋር በመሆን፤ በኢትዮጵያ የመገናኛ ብዙኃን ነፃነት እንዲረጋገጥ በሚደረገው ጥረት በጋራ እንዲሰሩም ጥሪውን አስተላልፏል፡፡
የማህበሩ ስራ አስፈጻሚ አባልና የህዝብ ግንኙነት ኃላፊው ጋዜጠኛ ዳዊት በጋሻው በባሕር ዳር በመከላከያ ኮማንዶዎች መያዙንና ወደ አዲስ አበባ መላኩን የዓይን እማኞች መግለፃቸው ይታወሳል።
[ ደመቀ ከበደ ፡ አዲስ አበባ ]