የኢትዮጵያ ዘውድ ምክር ቤት መስከረም 3, 2015 / ሴፕቴምበር 13, 2022 ባወጣው የሐዘን መግለጫ በዳግማዊት ንግሥት ኤልሳቤጥ ሕልፈተ ሕይወት የተሰማውን ጥልቅ ሐዘን ገለጠ።
በዘውድ ምክር ቤቱ ፕሬዚደንት ልዑል ኤርሚያስ ሣህለ ሥላሴ ኃይለ ሥላሴ አማካይነት ሐዘኑን የገለጠው ምክር ቤት፤ ንግሥት ኤልሳቤጥ ከኢትዮጵያ ጋር የነበራቸውን ጥልቅ ግንኙነትና ያበረከቷቸውንም አስተዋፅዖዎች ዋቤ ነቅሶ በማመላከት ነው።
አያይዞም፤ በንግሥቲቱ ሕልፈት ጥልቅ ሐዘን የገባው ቢሆንም፤ በሕይወት ሳሉ ለኢትዮጵያና ለግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ስላሳዩት ወዳጅነትና ዘላቂ ግንኙነት "በኢትዮጵያ ዘውድ ምክር ቤት ስም ልንዘክራቸው እንወዳለን" ብሏል።

The Crown Council of Ethiopia. Credit: CCE
የንግሥት ኤልሳቤጥን የኢትዮጵያ ጉዞ አስመልክቶም "ንግሥት ኤልሳቤጥ ኢትዮጵያን የጎበኙት አፄ ኃይለ ሥላሴን እጅ ለመንሳት፣ የምንወደውን ሕዝባችንን በዓይናቸው ለማየትና ለመጠየቅ እንዲሁም ውብና ለምለም አገራችንን ለመጎብኘት ነበር" ብሏል።

Queen Elizabeth II at the impressive Tissisal Falls, where the Blue Nile begins, with Emperor Haile Selassie during a royal visit to Ethiopia, February 1965. Credit: Hulton Archive/Getty Images
የኢትዮጵያ ዘውድ ምክር ቤት ፕሬዚደንት ልዑል ኤርሚያስ ሣህለ ሥላሴ ኃይለ ሥላሴ የ1967 መስከረም 2 መፈንቅለ መንግሥት ተከትሎ በቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ላይ ግድያ በመፈፀሙ ሳቢያ ወደ ኢትዮጵያ መመለስ ላልቻሉ ንጉሣዊ ቤተሰቦች ንግሥቲቱ ድጋፍ በማድረግ ዘላቂ የቤተሰብ ጓደኛና ባውለታ መሆናቸውን እንዳስመሰከሩ ጠቅሰዋል።
አያይዘውም "እኔ በግሌ የንግሥቲቱ ደግትና ቸርነት ተካፋይ ስለነበርኩህ በቅርበት ንግሥቲቱና የብሪታንያ ሕዝብ ለኢትዮጵያውያን ሰለሞናዊ የዘር ሐረግ ተወላጅ ዘመዶቻቸው አለኝታና ሰብሳቢም ጭምር እንደነበሩ ለመገንዘብ ችያለሁ" ብለዋል።
የዘውድ ምክር ቤቱ ፕሬዚደንት፤ ንጉሥ ቻርልስ ሳልሳዊ ንግሥት ኤልሳቤጥ ከኢትዮጵያ ጋር ስለነበራቸው ጥልቅ ግንኙነት ጠንቅቀው እንደሚያውቁ አመላክተው "እኛም የተወደዱ እናታቸውን ሲያጡ እንደ ቤተሰብ የሐዘናቸው ተካፋይ ነን" ሲል በምክር ቤቱ ስም የሐዘን ተጋሪነታቸውን ገልጠዋል።
በመጨረሻም "እግዚአብሔር የዳግማዊት ኤልሳቤጥን ነፍስ ይማርልን። ወደ ፈጣሪዎ ስንሸኝዎት ሐዘናችንን የምንገልጸው በዕንባ ነው። ረጅም ዕድሜ ለንጉሥ ቻርልስ 3ኛው ከመልካም ምኞትና ፀሎት ጋር እንመኛለን። እግዚአብሔር ኢትዮጵያን ለዘላለም ይባርክ" ብለዋል።