የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ 6ኛው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 2ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 8ኛ መደበኛ ስብሰባውን እያካሄደ ነው፡፡
ምክር ቤቱ በስብሰባው በጠቅላይ ሚኒስትሩ የቀረቡ ሹመቶችን መርምሮ እያፀደቀ ነው፡፡
በዚህም አቶ ቴዎድሮስ ምህረት ከበደ የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዚዳንት ሆነው ሲሾሙ ወ/ሮ አበባ እምቢያለ መንግሥቴ የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ምክትል ፕሬዚዳንት ሆነው ተሾመዋል፡፡
ተሿሚዎች በጉባኤው ፊት ቀርበው ቃለ-መሐላ ፈጽመዋል።
አቶ ቴዎድሮስ ምህረትና ወ/ሮ አበባ እምቢያለ በፕሬዚደንትና ምክትል ፕሬዚደንት የተሾሙት፤ የቀድሞዋ የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዚዳንት ወ/ሮ መዓዛ አሸናፊና የቀድሞው የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ምክትል ፕሬዚዳንት አቶ ሰለሞን አረዳ ዛሬ ማክሰኞ ጥር 9 በፈቃዳቸው የሥራ መልቀቂያ ደብዳቤ ለምክር ቤቱ ማስገባታቸውን ተከትሎ ነው።

አቶ ቴዎድሮስ አዲሱን የሥራ ኃላፊነታቸውን ከመቀበላቸው በፊት በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ሕግ ትምህርት ቤት መምህርና ነገረ ፈጅ ነበሩ። የኢትዮጵያ የሕግ ባለ ሙያዎች ማኅበርንም በፕሬዚደንትነት አገልግለዋል።
በምክትል የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ምክትል ፕሬዚዳንትነት ቃለ መሐላ የፈፀሙት ወ/ሮ አበባ እምቢያለ በፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ፣ በፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤትና በፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት በዳኝነት ሠርተዋል።

