የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ባለሥልጣን 36ኛውን የአፍሪካ ህብረት የመሪዎች ጉባዔ ለሚዘግቡ የሀገር ውስጥ እና የውጭ ጋዜጠኞች የመግቢያ ባጅ መስጠትን ጨምሮ ሌሎች ምቹ ሁኔታዎች በመፍጠር ላይ መሆኑን አስታወቀ።
ባለሥልጣኑ እስካሁን ድረስ በጉባዔው ላይ ተገኝተው የዘገባ ስራ ለመስራት ላመለከቱ ለ852 ጋዜጠኞች የመግቢያ ባጅ የሰጠ ሲሆን፥ ከእነዚህም ውስጥ 332ቱ የሀገር ውስጥ እንዲሁም 70ዎቹ ተቅማጭነታችውን ኢትዮጵያ ያደረጉ የውጭ ሀገራት መገናኛ ብዙኃን የዜና ወኪሎች ናቸው።
ከዚህ ባለፈም 450ዎቹ ከተለያዩ ሀገራት የመጡ የውጭ ሀገራት መገናኛ ብዙኃን ጊዜያዊ የዜና ወኪሎች መሆናቸውንም አስታውቋል።
ባለሥልጣኑ እንደ ከዚህ ቀደሙ ሁሉ ጋዜጠኞች ከውጭ ይዘዋቸው የሚመጡትን የብሮድካስት መሳሪያዎች ወደ ሀገር ውስጥ ከቀረፅ ነፃ እንዲያስገቡ እና የቪዛ አገልግሎት እንዲያገኙ የ24 ሰዓት ፈጣን አገልግሎት እየሰጠ መሆኑንም ጠቅሷል።
ለአገልግሎቱ ቅልጥፍናም ከኢትዮጵያ አየር መንገድ፣ ከጉምሩክ ኮሚሽን፣ ከኢሚግሬሽን ዜግነት እና ወሳኝ ኩነት ኤጀንሲ፣ ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር እና ከአፍሪካ ህብረት ጋር በትብብር በመስራት ላይ ይገኛል።
በቀጣይም ባለሥልጣኑ ጉባዔው እስከሚጠናቀቅ ድረስ በቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያና በአፍሪካ ህብረት በሚገኙ ጊዜያዊ ቢሮዎቹ እንዲሁም ፍላሚንጎ አካባቢ ከኤግዚቪሽን ማዕከል ጀርባ በሚገኘው ዋናው መስሪያ ቤት አገልግሎት እንደሚሰጥም ነው ያስታወቀው።