የዳግማዊት ንግሥት ኤልሳቤጥ አስከሬን ትናንት ዊንድዘር ቤተመንግሥት በሚገኘው የቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተፀሎት ከባለቤታቸው ልዑል ፊሊፕ፣ ከአባታቸው ንጉሥ ጆርጅ አራተኛ፣ ከንግሥት እናትና እህት ማርጋሬት አስከሬኖች ጎን አረፈ።
የዊንድዘር ዲን የቀብሩን ሥነ ሥርዓት መርተዋል።
በዕለቱም የኢትዮጵያን ፕሬዚደንት ሳህለ ወርቅ ዘውዴን አክሎ ከመላው ዓለም የተጋበዙ መሪዎች በሥፍራው ተገኝተዋል፣ በሺህዎች የሚቆጠሩ ዜጎች በጎዳናዎች ላይ ተገኝተው የንግሥቲቱ አስከሬን ሲያልፍ የመጨረሻ ስንብት አድርገዋል።
በመላው ዓለምም በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ የቀብር ሥነ ሥርዓቱን በቴሌቪዥን ተከታትለዋል።
ብሔራዊ የሐዘን ቀን
ይህ በእንዲህ እንዳለም፤ የፊታችን ሐሙስ አውስትራሊያ ውስጥ የዳግማዊት ንግሥት ኤልሳቤጥን ዕረፍት ለመዘከር ብሔራዊ የሐዘን ቀን ሆኖ ይውላል።
በሥነ ሥርዓቱ ላይ ለመገኘት ጠቅላይ ሚኒስትር አንቶኒ አልባኒዚ ከለንደን ወደ አውስትራሊያ ያቀናሉ።
የብሔራዊ መታሰቢያ ሥነ ሥርዓቱ በቀጥታ ከካንብራ ፓርላማ ለሕዝብ ይሰራጫል።
ሰብዓዊ መብቶች
የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) መስከረም 7 - 2015 ባወጣው መግለጫ ከትግራይ ክልልና ከአዋሳኝ የአማራ ክልል አካባቢዎች ተፈናቅለው በአዋሽ ሰባት የተያዙ ስዎች የመንቀሳቀስ መብት በአፋጣኝ ሊከበር እንደሚገባ አሳሰበ።
ኮሚሽኑ በአማራ ክልል በደቡብ ወሎ ዞን ከጃሬ የተፈናቃይ መጠለያ ጣቢያ እንዲሁም ከመሃል ትግራይ መቀሌ፣ አዲግራት፣አክሱም፣ ሽሬ ከተሞች ወደ አዋሽ ሰባት የፌዴራል ፖሊስ ማሰልጠኛ እንዲዘዋወሩ የተደረጉ መሆኑን ጠቅሷል።።
አክሎም፤ የተፈናቃዮችን ሁኔታ ከግንቦት ወር 2014 ዓ.ም. ጀምሮ ክትትል ሲያደርግ እንደቆየና መጠለያ ጣቢያው በአብዛኛው የትግራይ ተወላጆች የሆኑ እና ከመሀል ትግራይ ከተሞች እና አካባቢው ተፈናቅለው የመጡ በወቅቱ 2,800 የሚሆኑ ሰዎች የሚገኙበት እንደነበር አመልክቷል።
ይህንኑ አስመልክቶም የኢሰመኮ ዋና ኮሚሽነር ዶ/ር ዳንኤል በቀለ "ለሕዝብ ጸጥታ፣ ደኅንነት እና ጤና ወይም የተፈናቃዮችን ደኅንነት ለማስጠበቅ ሲባል በተፈናቃዮች እንቅስቃሴ ላይ ገደብ ሊጣል የሚችልበት ሁኔታ ቢኖርም፤ የዚህ አይነቱ ገደብ የአስፈላጊነት፣ ምክንያታዊነት እና ተመጣጣኝነት መርሆችን በጥብቅ በተከተለ መንገድ ሊከናወን የሚገባው መሆኑን
አሳስበው “በአዋሽ ሰባት የፌዴራል ፖሊስ ማሰልጠኛ ውስጥ የሚገኙ ተፈናቃዮች የመጡባቸውን የትግራይ ክልል አካባቢዎች ብቻ መሰረት በማድረግ ለተራዘመ ጊዜ የመንቀሳቀስ ነጻነታቸውን ተነፍገው እንዲቆዩ መደረጉ የአስፈላጊነት፣ምክንያታዊነት እና የተመጣጣኝነት መርሆዎችን የሚቃረን ነው” ብለዋል።
በሌላም በኩል፤ በተባበሩት መንግሥታት ሰሜን ኢትዮጵያ ውስጥ ተጥሰዋል የተባሉ ሰብዓዊ መብቶች ሁኔታዎችንና በተያያዥነትም ተፈፅመዋል የተባሉ ጉዳዮችን ለማጣራት ባለፈው ዓመት የተቋቋመው ኮሚሽን የባለሙያዎች ቡድን የኢትዮጵያ መንግሥትና ሽርካዎቹ የትግራይ ሕዝብ እንደ ኢንተርኔት፣ ባንክና መብራት የመሳሰሉ መሠረታዊ ግልጋሎቶችን መንፈጋቸውን አመልክቷል።
የኮሚሽኑ ሰብሳቢ የሆኑት ካሪ ቤቲ ሙሩንጊ "የፌዴራል መንግሥቱ ማስራብን እንደ አንድ የጦርነት ዘዴ ይጠቀምበታል የሚል አመኔታን የሚያሳድርብን ምክንያታዊ አስባቦች አሉን" ብለዋል።
አያይዘውም፤ ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ዓይኖቹን ከመጨፈን ይልቅ ግጭቶች እንዲቆሙና አገልግሎቶችም እንዲቀጥሉ የድርሻውን እንዲወጣ ጥሪ አድርገዋል።
የኮሚሽኑን ሪፖርት አስመልክቶ በሕወሓት በኩል ድጋፍን ሲያገኝ በመንግሥት በኩል ተቃውሞ ገጥሞታል።