በሰሜን ኢትዮጵያ ትግራይ ክልል ውስጥ በመንግሥትና የሕወሓት ወታደሮች መካከል ከመለስተኛ ግጭት ወደ ሙሉ ጦርነት ከፍ ማለቱን የተለያዩ የመረጃ ምንጮች እየገለጡ ነው።
ሙሉ ወታደራዊ ግጭቱ ዛሬ ስለ መጀመሩ ካመላከቱት ሪፖርቶች ውስጥ አንዱ የሕወሓት ቃል አቀባይ አቶ ጌታቸው ረዳ ናቸው።
ቃል አቀባዩ ከተከዜ እስከ ኢሮብ ባሉ ግንባሮች በኤርትራ ወታደሮች ሙሉ ጥቃቶች መካሔዳቸውን ያመላከቱ ሲሆን፤ በማይ ኩኽሊ፣ ዝባን ገደና፣ አዲአዋላ፣ ራማ፣ ፀሮናና ዛላአንበሳ በኩል ከባድ ውጊያዎች መካሔዳቸው ጠቁመዋል።
አያይዘውም፤ የኢትዮጵያ መንግሥት ምሥራቃዊና ሰሜናዊ ዕዞች፣ ሶስት የኮማንዶ ክፍለ ጦሮች፣ የአማራ ልዩ ኃይልና ፋኖ ተዋጊዎች መሳተፋቸውን ገልጠዋል።
በሌላም በኩል የኤርትራን ጦር እንቅስቃሴዎች አሜሪካ ክትትል እያደረገች ስለመሆኑ የዩናይትድ ስቴትስ የምሥራቅ አፍሪካ ልዩ ልዑክ ማይክ ሐመር ተናግረዋል።
ይሁንና በኢትዮጵያና ኤርትራ መንግሥታት በኩል የተሰጠ ይፋዊ መግለጫ የለም።
ሌሎች ሪፖርቶች እንደሚያመለክቱት ከሆነም አዲርቃይን ጨምሮ ቀደም ሲል በሕወሓት ቁጥጥር ስር የነበሩ ሥፍራዎች በኢትዮጵያ መከላከያና አጋር ኃይሎች እጅ መግባቱ በመንግሥታዊ ብዙኅን መገናኛዎች ውስን በሆነ መልኩ እየተገለጡ ነው።
ሰብዓዊ መብቶች
በተባበሩት መንግሥታት ሰሜን ኢትዮጵያ ውስጥ ተጥሰዋል የተባሉ ሰብዓዊ መብቶችን ለመመልከት ባለፍው ዓመት የተሰየመው የሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን የባለሙያዎች ቡድን የኢትዮጵያ መንግሥትና ሽርካዎቹ የትግራይ ሕዝብ እንደ ኢንተርኔት፣ ባንክና መብራት የመሳሰሉ መሠረታዊ ግልጋሎቶችን መንፈጋቸውን ይፋ ባደረገው ሪፖርቱ አመልክቷል።
የኮሚሽኑ ሰብሳቢ የሆኑት ካሪ ቤቲ ሙሩንጊ "የፌዴራል መንግሥቱ ማስራብን እንደ አንድ የጦርነት ዘዴ ይጠቀምበታል የሚል አመኔታን የሚያሳድርብን ምክንያታዊ አስባቦች አሉን" ብለዋል።
አያይዘውም፤ ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ዓይኖቹን ከመጨፈን ይልቅ ግጭቶች እንዲቆሙና አገልግሎቶችም እንዲቀጥሉ የድርሻውን እንዲወጣ ጥሪ አድርገዋል።
የኮሚሽኑን ሪፖርት አስመልክቶ በሕወሓት በኩል ድጋፍን ሲያገኝ በመንግሥት በኩል ሙያዊ መሥፈርቶች የጎደለው ሪፖርት አድርጎ በመልከት የተቃውሞ ድምፅ አሰምቶበታል።
የኢትዮጵያ መንግሥት ይልቁንም 3,600 ያህል የአማራና አፋር ነዋሪዎች ላይ ከሴፕቴምበር 2021 እስከ ጃኑዋሪ 2022 በሕወሓት የጅምላ ግድያ ተፈጽሞባቸዋል ሲል በመንግሥታዊ ሪፖርቱ ከስሷል።