ለዳግማዊት ንግሥት ኤልሳቤጥ ዝክረ መታሰቢያ ይፋ የሐዘን መግለጫ ለማውጣትና የንጉሥ ቻርልስ ሳልሳዊን የዙፋን ውርስ ዕውቅና ለመቸር ዛሬ የተሰየመው የአውስትራሊያ ፓርላማ ሪፐብሊክ የማቆም ክርክርንም አስተናግዷል።
የአውስትራሊያ ግሪንስ ፓርቲ መሪ አዳም ባንድት አውስትራሊያውያን ከዚህ ዓለም በሞት ለተለዩት ንግሥት ኤልሳቤጥ ከበሬታ የተመላው ሐዘናቸውን በመግለጥ ወደ ሪፐብሊክ ማምራት እንደሚሹ አመላክተዋል።
ወቅቱም አውስትራሊያውያን በሳልነታቸውን የሚያሳዩበትና ወደ ፊት የመራመጃቸው ጊዜ መሆኑን በማንሳት "የእዚህች አገር ርዕሰ ብሔር በሕዝብ፣ ለሕዝብና ከሕዝብ ሊመረጥ ይገባል" ብለዋል።

Greens leader Adam Bandt says people can share their sympathy about the death of Queen Elizabeth II and still have conversations about whether a constitutional monarchy is right for Australia. Credit: Sam Mooy/Getty Images

Senator Sarah Hanson-Young. Credit: Tracey Nearmy/Getty Images
"የእኛ ርዕሰ ብሔር መሆን ያለበት የእኛ የሆነ አውስትራሊያዊ ነው" ሲሉ ለሕግ መወሰኛ ምክር ቤቱ አሰምተዋል።
ይህ በእንዲህ እንዳለም፤ የአውስትራሊያ ሪፐብሊክ ንቅናቄ የንግሥቲቱን የቀብር ሥነ ሥርዓትና ብሔራዊ የሐዘን ቀን ፍፃሜን ተከትሎ ከዘውዳዊ ሥርዓት ለመላቀቅ ጊዜ መጥፋት እንደሌለበት የንቅናቄው ሊቀመንበር ፒተር ፊትዝመንስ አሳስበዋል።
አክለውም "በውልደት መብት መግዛት፤ በአውስትራሊያ ዲሞክራሲ ውስጥ ሥፍራ የለውም" ብለዋል።
"ዕሳቤው እንደ ዘውዳዊ ሥርዓቱ ሁሉ ለአውስትራሊያውያን ዕሴቶች ባዕድ ነው። ማንም ሰው ለውጭ ንጉሥ ወይም ርዕሰ ብሔር የታማኝነት ቃል ኪዳን ሊፈጽም አይገባም" ብለዋል።
የአውስትራሊያ ነባር ዜጎች የምክር ቤት አባላትም በበኩላቸው የንግሥቲቱ ሕልፈተ ሕይወትና የቅኝ ግዛት አሻራ አሳድሮባቸው ያለውን ስሜት በተዛነቀ መንፈስ ገልጠዋል።
የሪፐብሊክ ምሥረታ ደጋፊና ዓላማውንም አራማጅ የሆኑ የአውስትራሊያ ጠቅላይ ሚኒስትር አንቶኒ አልባኒዚ የንግሥቲቱን ሞት ተከትሎ ፈጥነው የሪፐብሊክ ክርክርን ማንሳት እንደማይሹ በተደጋጋሚ ገልጠዋል።