የዛሬዋ ዕለት ፌብሪዋሪ 24 የሩስያው ፕሬዚደንት ቭላድሚር ፑቲን 200,000 ያህል ጦራቸው ዩክሬይንን እንዲወር ትዕዛዝ የሰጡበት አንደኛ ዓመት ሆኖ ተቆጥሯል።
በዓለም ዙሪያ ያሉ በርካታ አገራትም አጋርነታቸውን ለዩክሬይን ገልጠዋል።
በተባበሩት መንግሥታት ግምት ጦርነቱ ከተጀመረ አንስቶ 7,000 ሰላማዊ የዩክሬን ነዋሪዎች ሕይወታቸውን ማጣቸው ተጠቁሟል።
የዩክሬይን መከላከያ ሚኒስቴር እንዳመለከውም፤ ከ130,000 በላይ ሩስያውያን ወታደሮች ሕይወት በጦር ግንባር አልፏል።
የሩስያና ዩከሬይን ጦርነትን አንደኛ ዓመትን ተከትሎ የአውስትራሊያ ፌዴራል መንግሥት የ$33 ሚሊየን ዶላርስ ወታደራዊ እገዛ ለማድረግ ቃል ገብቷል።
ወታደራዊ እርዳታው የቅኝት ድሮኖች መላክን ያጠቃልላል።
ጠቅላይ ሚኒስትር አንቶኒ አልባኒዚ ዩክሬይን ውስጥ የጦር ወንጀሎች መፈጸማቸው አስመልክቶ ምንም ጥርጣሬ የሌለው ጉዳይ መሆኑን አመላክተዋል።
ይህ በእንዲህ እንዳለም፤የአውስትራሊያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ፔኒ ዎንግ፤ ቻይና የዩክሬይን ጦርነት እንዲያበቃ እንጂ እንዲባባስ አስተዋፅዖ እንዳታደርግ አሳስበዋል።
ለውጭ ጉዳይ ሚኒስትሯ አስተያየት መነሻ የሆነውም ቻይና ለሩስያ የጦር መሳሪያዎችን ለማቅረብ እያሰበች ነው የሚሉትን ሪፖርቶች ተከትሎ፤ የኔቶ ዋና ፀሐፊ ሄንስ ስቶልቴንበርግ በአጋር አገራት በኩል ቤጂንግ ጦር መሳሪያዎችን ለሩስያ የማቀበል አዝማሚያ ያላት ስለመሆኑ ፍንጮች መኖራቸውንና ማስጠንቀቂያም ለቤጂንግ መሰጠቱን መግለጣቸውን ተከትሎ ነው።
ካንብራና ቤጂንግ
የካንብራና ቤጂንግ ከፍተኛ ባለ ስልጣናትን ሐሙስ ዕለት በበይነ መረብ ያካሔዱትን "ፍሬያማ" ስብሰባ ተከትሎ ቻይና አውስትራሊያ ላይ ጥላቸው ያሉት ምጣኔ ሃብታዊ ማዕቀቦች በሳምንት ጊዜያት ውስጥ ሊነሱ ነው።
ይህንኑም እውን ለማድረግ የአውስትራሊያ ንግድ ሚኒስትር ዶን ፋሬል በመጪዎቹ ሳምንታት ውስጥ በጢያራ ተሳፍረው ቤጂንግ እንደሚዘልቁ የአውስትራሊያ መንግሥት ምንጮች ለSBS News ጠቁመዋል።
በአውስትራሊያ መንግሥት በኩል የእዚህ ዓይነቱ ጉብኝት በዓመት 20 ቢሊየን የሚያስገኘው ንግድ ዕቀባ መነሳት ይፋ መግለጫ የሚሰጥበት ጊዜ ነው የሚል ዕሳቤ አለ።