1. የግልና የፓርቲ አጀንዳዎቻችንን ለጊዜው ወደጎን በማስቀመጥ የሀገርን ህልውና እና የህዝብን ሕይወት መታደግ የውዴታ ግዴታችን መሆኑን አበክረን እንገልፃለን፡፡ በዚህ ቀን ያበቃል ብሎ መወሰን የማይቻለው የኮቪድ 19 ችግር እስከሚያበቃ ከዚያም እስከ ምርጫው ድረስ አሁን ያለው መንግሥት እንዲቀጥል ኢሕአፓ ስምምነቱን ይገልፃል፡፡ በእያንዳንዱ ሀገርን የማዳን እና የሕዝባችንን ጤንነትና ሕይወት የመታደግ ሥራ ውስጥ ከመንግሥት ጎን እንደምንሰለፍ ስንገልጽ መንግሥትን ለመገዳደርም ሆነ የተጠቀሱትን ሀገራዊ ቅቡልነት ያላቸው ተግባሮች ለማደናቀፍ የሚወሰዱ እና ሀገርን የሚጎዱ ማናቸውንም በእልህና በማን አለብኝነት ላይ የተመሠረቱ እርምጃዎችን እንቃወማለን፡፡
2. የወረርሽኙ መስፋፋትና እድገት፣ እያደረሰው ያለው ጉዳት፣ እየቀነሰ መጥቶ፣ ሁኔታዎች ፍፃሜውን ሲያመላክቱ፣ ቀጣዩ ምርጫ መቼ እንደሚካሄድ በሚደረገው ውሳኔ ላይ ተፎካካሪ ፓርቲዎች የሚኖራቸውን ተሳትፎ ባለመገደብ፣ ገዥው ፓርቲ “እኔ በምቀድላችሁ ቦይ ፍሰሱ” ከሚል አካሄድ በተላቀቀ መልኩ፣ ከራሱ ውጭ ካሉት የፖለቲካ ሃይሎች ጋር በዕውነተኛ ተፎካካሪነት ላይ የተመሠረተ ምክክር እንዲያደርግና የጋራ ውሳኔ እንዲሰጥ አበክረን እንጠይቃለን፡፡
3. በዚህ ሂደት ውስጥ፣ ወረርሽኙ ተግትቶ፣ ሀገራችንም ህልውናዋን ጠብቃ፣ የምርጫ ዝግጅት በሚደረግበት ወቅት፣ ገዥው ፓርቲ እንደተለመደው የመንግሥት ስልጣኑን ለፖለቲካዊ ፍጆታ ማዋሉን እንዳይቀጥል አበክረን እናሳስባለን፡፡ በተፈጠረው አጋጣሚ በመጠቀም የሚያካሂዳቸውን የምረጡኝ ዓይነት ስውር ቅስቀሳዎች እንዲያቋርጥና የተጣለበትን ሀገር የማዳን ሃላፊነት እንዲወጣ እንጠይቃለን፡፡ ይህንን ስንል በከፍተኛ የስልጣን እርከን ላይ ብቻ ሳይሆን እስከወረዳ ያለውን መዋቅርም በማካተት ነው፡፡ መንግሥት አስቸኳይ/አሳሳቢ ጉዳዮችን በተመለከተ “አጣርተን እንገልፃለን” ከማለት ባለፈ በተግባር ሲገልጽ አይደመጥም (ለምሳሌ ደምቢዶሎ እንደታገቱ ደብዛቸው ስለጠፋው ተማሪዎች) በመሆኑም ተመሳሳይ ጉዳዮችን ለህዝብ የማሳወቅ ልምዱን እንዲፈትሽ ያስፈልጋል፡፡ በተጨማሪም በየወረዳው በሚንቀሳቀሱ አባሎቻችን ላይ የሚደርሰው መዋከብ፣ በአንዳንድ ሥፍራዎች የሚያጋጥሙ እስራቶች በአስቸኳይ እንዲቆሙ፤ የታሰሩትም እንዲፈቱ እንጠይቃለን፡፡
4. በመጨረሻም የሀገርን አንድነትና የሕዝብን ደህንነት በማስቀደም ፖለቲካ ውስጥ አብሮ ለመሥራት ከሚፈልጉ የፖለቲካ ፓርቲዎች፣ ሲቪክ ድርጅቶች እና ግለሰቦች ጋር ለመሥራት ኢሕአፓ ሙሉ ፈቃደኛ መሆኑን እንገልፃለን፡፡
ፈጣሪ ኢትዮጵያን ይባርክ!