አገረ ሱዳን የሉዓላዊ የሽግግር ምክር ቤቷንና የሚኒስትሮች የጋራ ምክር ቤቷን ሰብስባ የዲፕሎማሲ ጫና ለመፍጠር ወደ ተለያዩ አገራት የመሄድ ተገቢነት አስወስናለች።
እንደ አልዓይንና ሌሎች የአረብ ሚዲያዎች ዘገባ የካርቱም ፖለቲከኞች ወደላይ ወደ ካይሮ፣ ወደ ጎን ወደ አስመራ፣ ወደ ታችም ወደ ጁባ እንዲሁም ባሻጋሪ ወደ ሳዑዲ አረቢያ በመሄድ ጉዳዩን እያስረዱ ነው።
~ የሉዓላዊ ሽግግር ምክር ቤቱ አባል ሌፍተናንት ጄነራል ሻምሰዲን ካባሺ በደቡብ ሱዳን፣
~ የሉዓላዊ ሽግግር ምክር ቤቱ ምክትል ሊቀመንበር ሌፍተናንት ጄነራል መሐመድ ሃምዳን ዳጋሎ ወደ ኤርትራ፣
~ የሉዓላዊ ሽግግር ምክር ቤቱ አባል ሌፍተናንት ጄነራል ኢብራሂም ጃቢር ወደ ቻድ፣
~ መሐመድ ፋኪ ሱሌማን ወደ ሳዑዲ አረቢያ ጉብኝት አድርገዋል፡፡
~ ተጠባባቂ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ኦማር ቀመረዲን፣ የስለላ ኃላፊው ጄነራል ጃማል አዲን ኦማር ፣የማስታወቂያ ሚኒስትሩ ፋይሳል መሐመድ ሳሊህ እና የሉዓላዊ ሽግግር ምክር ቤቱ አባል ሌፍተናንት ጄነራል ሻምስ ኢል ዲን ካባሺን ያካተተው ሌላው ቡድን ደግሞ ዛሬ ወደ ካይሮ ከትመዋል።
በግልባጩ የኢትዮጵያ መንግስት ትናንት በጁባ የቀድሞውን ጠሚር ኃይለማሪያም ደሳለኝን ልኳል። በካርቱም ያሉት አምባሳደር ይበልጣል አዕምሮም መቀመጫቸውን ካርቱም ላደረጉ የዲፕሎማቲክ ማህበረሰብ አባላት "ተወረናል ፣ ድርድር ይበጀናል" ሲሉ ለማስረዳት ጥረዋል።
አሥመራ ደግሞ የግብፁን አምባሳደር በኢትዮጵያ አየር መንገድ ቻርተርድ ተኮናትራ ወደ አገሩ ልካለች።
ግብፅ ሱዳን ምንም ብትጠይቀኝ ከጎኗ እሰለፋለሁ ብላ ከለፈፈች ሰንብታለች።
ወዲህ አየር ክልሌን ጥሶ የኢትዮጵያ ሔሊኮተር በርሮ ነበር ስትል ካርቱም ዜና ለቃለች ፣ ባይረጋገጥም ቅሉ የሱዳን የጦር ሔሊኮፕተርም ከአየር ወርዶ መሬት ላይ መነጠፉ ተወርቷል።
የደቡብ ሱዳን ከብት አርቢዎች ድንበር ጥሰው ጋምቤላ ገብተዋል በሚል ወጠርጠርጠር ያለ ነገር ተሰምቷል።
ቀጠናው ሰላሙ እየቀጠነ ይመስላል።
እንዲያም ሆኖ በመተከል ፣ በትግራይ ፣ በወለጋ ሠላም ያጣቺው አገር የቀጠናውን ጉዳይ አላጮኸውም ብላለች። ቃል አቀባዩ አምሳደር ዲና ሙፍቲ “ኢትዮጵያ ይህንን ችግር ማጉላት ያልፈለገችው ጉዳዩን ቀጠናዊ ላለማድረግ ነው” ማለታቸው ይታወሳል።