"ከ 440ዎቹ የምርጫ ክልሎች ውጤት ያሳወቁት 221ዱ ናቸው " የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ

*** "ቦርዱ ከምርጫ ክልሎች የሚደርሰው ውጤት ከዘገየና በዋና ፅህፈት ቤቱ የሚከናወነው የማጣራት ሂደት ጊዜ ከወሰደ እስከ ሃያ ቀን ባለው ጊዜ ጊዜያዊ ውጤት ያሳውቃል" - ሶልያና ሽመልስ

SBS Amharic

Solyana Shimelis, spokeswoman of the National Electoral Board of Ethiopia. Source: SBS Amharic/Demeke Kebede

ባለፉት ቀናት ሰኞና ማክሰኞ ማለትም ሰኔ 14 እና 15 / 2013 ዓም በተከናወነው ምርጫ ለተወካዮች ምክር ቤትና ለክልል ምክር ቤቶች የተወዳደሩ ዕጩዎችን የምርጫ ውጤት በአምስት ቀናት ውስጥ ውጤት እንደሚያሳውቁ የቦርዱ መመሪያ ይገልፃል።

በዚህ መሰረት ዛሬ ብዙዎቹ ምርጫ ጣቢያዎች ውጤት እንደሚለጥፉ ቢጠበቅም ከ 440ዎቹ ምርጫ ክልሎች ውስጥ 221 ዱ ናቸው ውጤት እንደለጠፉ የተረጋገጠው ሲሉ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ኮሙኒኬሽን ኃላፊ ወይዘሪት ሶልያና ሽመልስ ለጋዜጠኞች አሳውቀዋል።

ሶልያና እንዳሉት ምርጫ ከተከናወነባቸው መካከል በኦሮሚያ ክልል ከ171 ዱ ውስጥ 125 የምርጫ ክልሎች ውጤት የለጠፉ ሲሆን በአማራ ክልል ከ125ቱ  ውስጥ የ40 የምርጫ ክልሎች ፣ በአዲስ አበባ ደግሞ ከ23 ቱ  ውስጥ 10 ሩ ምርጫ ክልሎች ውጤት አሳውቀዋል ብለዋል።

ለቦርዱ ዋና ፅህፈት ቤት 7 የምርጫ ክልሎች ውጤት ያስገቡና የማረጋገጫ ምስክር ወረቀት የተሰጣቸው ቢሆንም  ከፓርቲዎች የሚመጡ ቅሬታዎች እየተቀበልን በመሆኑ ሲጠናቀቁ ይፋ እናደርጋለን ብለዋል ሶልያና።

ለምርጫ ክልሎች ውጤት ማሳወቅ መዘግየት ምክንያቱ እንደየክልሎች የተለያዩ ቢሆንም የትራንስፖርት ችግር፣ በታችኞቹ የምርጫ ጣቢያዎች ተጣርተው የሚቀርቡ ውጤቶች ለምርጫ ክልሎች ዘግይተው እየደረሱ መሆን  ለምርጫ ክልሎቹ የማጣራት ሂደትና ውጤት ማሳወቅ ጊዜ ለመውሰድ ምክንያቶች ናቸው ብለዋል።

በምርጫ ወረቀቶች መዘግየት የተነሳ ሰኔ 15/2013 ዓም ጭምር የምርጫ ክንውን ያደረጉት ጋምቤላና ሲዳማ ክልሎች የቆጠራና ድመራ ሂደታቸውን እያከናወኑ ነው ብለዋል።

ቦርዱ ከምርጫ ክልሎች የሚደርሰው ውጤት ከዘገየና በዋና ፅህፈት ቤቱ የሚከናወነው የማጣራት ሂደት ጊዜ ከወሰደ እስከ ሃያ ቀን ባለው ጊዜ ጊዜያዊ ውጤት ያሳውቃል ነው ያሉት።

በሌላ በኩል በድሬደዋ 6 የምርጫ ጣቢያዎች ለክልል ምክር ቤትና አንድ የምርጫ ክልል ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ምርጫ ሳይከናወን ቀርቷል ብለዋል ሶልያና ፤ ለዚህም ምክንያቱ የምርጫ ወረቀት መዘግየቱ እንደሆነ ከምርጫ አስፈፃሚዎች በቅርቡ ይፋ እንደተደረገላቸው አሳውቀዋል። ለዚህ ችግር ተጠያቂ የሚሆኑ አካላትን እያጣራን ነው ያሉት የኮሙኒኬሽን ኃላፊዋ የቦርዱን ውሳኔም እናሳውቃለን ሲሉ አስረድተዋል።

ሶልያና በፓርቲዎች እየቀረቡ ያሉ ቅሬታዎች በሁለት ቀናት ውስጥ ተጠቃሎ እንዲቀርብላቸውም አሳስበዋል።

[ ደመቀ ከበደ ፡ አዲስ አበባ ]


2 min read

Published

By Demeke Kebede


Share this with family and friends


Follow SBS Amharic

Download our apps

Watch on SBS

SBS World News

Take a global view with Australia's most comprehensive world news service

Watch now