በኮቪድ 19 እና በፀጥታ ስጋት ምክንያት ለሁለት ጊዜያት ተራዝሞ የነበረው የነበረው 6ኛው የኢትዮጵያ ምርጫ ሰኔ 14 ቀን 2013 ዓም ተከናውኗል። በፀጥታ መደፍረስ ውስጥ ባለው የትግራይ ክልል እና ለጳጉሜ 1 ቀን እንዲመርጡ ከተወሰነባቸው 69 የምርጫ አካባቢዎች በስተቀር በመላው አገሪቱ ተከናውኗል።
ከ44 ሺህ በላይ የአገር ውስጥና ከ200 በላይ የውጭ አገራት ታዛቢዎች የታዘቡት መሆኑ የተገለፀው ምርጫ "ይህ ነው የሚባል የጸጥታ ችግር ሳያጋጥም ተጠናቋል" ብለዋል የቦርዱ ሰብሳቢ ወይዘሪት ብርቱካን ሚደቅሳ።
እንደ ሰብሳቢዋ ገለፃ "በአማራ ክልል አንድ ምርጫ ጣቢያ ላይ ሰዎች እርስ በእስር ተጋጭተው ተቋርጦ ነበረ፤ በአማራ ክልለ አንድ ጣቢያ ላይ የአስተዳደር አካላት ገብተው አንወጣም በማለታቸው፤ ቦርዱ አስፈጻሚ ለቆ ወጥቶ ነበረ። ግን የምርጫው ሰላማዊነት በጣም በመልካም ሁኔታ ተጠናቋል፤ የከፋ የፀጥታ ችግር አልገጠመንም" ብለዋል።
በኦሮሚያ ክልል ደግሞ " አንዳንድ የምርጫ ክልሎች የፀጥታ ችግር አለባቸው ተብለው ተለይተው የነበሩ፤ ከስጋት የተነሳ ያልተከፈቱ ነበሩ። ምስራቅ ሀረርጌ ፉኛ ጊራ ምርጫ ክልል የተወሰኑ ጣቢያዎች ያልተከፈቱ ነበሩ፣ ምእራብ ሸዋ ናኖ በሁለት ጣቢያዎች ላይ ታጣቂዎች የምርጫ ሂደቱን ለመረበሽ ሞክረው ነበረ።" ብለዋል።
በአዲስ አበባ አጋጥሞ የነበረውን የድምጽ መስጫ ወረቀት እጥረት ለመቅረፍ ቀኑን ሙሉ ተሰርቷል ያሉት ወይዘሪት ብርቱካን በሲዳማ ክልል ካጋጠመ የምርጫ ቁሳቁስ እጥረት ጋር በተያያዘ ጊዜ በመገፋቱ ቦርዱ በ1162 የምርጫ አዋጁ መሰረት ምርጫው እንዲቋረጥ ተደርጓል፤ ቁሳቁስ ከተሰራጨ በኋላ ነገ ከቀኑ 5 ሰዓት ጀምሮ በሲዳማ በ19 የምርጫ ክልሎች በሙሉ ይቀጥላል" ብለዋል።
በቤኒሻንጉል ጉምዝ፣ እና በጋምቤላም በተወሰኑ ምርጫ ጣቢያዎች በድምጽ መስጫ እጥረት ምክንያት ምርጫው ተቋርጧል፤ ነገ የምርጫ ቁሳቁስ ከደረሰ በኋላ መቼ እንደሚቀጥል ይወሰናል ያሉ ሲሆን በአጠቃላይ በዚህ 6ኛው አገራዊ ምርጫ ውሎ በተወሰኑ ምርጫ ጣቢያዎች ላይ የአስፈፃሚ ችግሮች እና ውስንነቶች ታይተዋል ብለዋል። ለዚህም ይቅርታ ጠይቀዋል። ህዝቡ አመቺ ባልሆነ ሁኔታ ውስጥ ሆኖ ተሰልፎ ሲመርጥ በመዋሉ ምስጋናም አቅርበዋል።
የምርጫ ውጤቶች ከስንት ሰዓት በኋላ መታወቅ እንደሚጀመሩ ከኤስ ቢኤስ አማርኛ ለቀረበላቸው ጥያቄ ምላሽ የሰጡት ወይዘሪት ብርቱካን ከዛሬ ሌሊት ጀምሮ ቆጠራ በሚያጠናቅቁ ምርጫ ጣቢያዎች መግለፅ ይጀመራል፣ በቦርዱ አጠቃላይ ጊዜያዊ ውጤት ቢበዛ በአስር ቀን ውስጥ እናሳውቃለን ሲሉ መልሰዋል።

Members of the National Electoral Board explain how ballots are counted in front of observers after polls closed in Addis Ababa, on June 21, 2021. Source: Getty
ደመቀ ከበደ ፡ አዲስ አበባ