ኦሮሚያ - የሞትና አካል ጉዳት አደጋ በተቃውሞ ሰልፎች

የኢሰመኮ ጋዜጣዊ መግለጫ

EHRC

Source: Courtesy of EHRC

የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን በኦሮሚያ ለተቃውሞ በተጠሩ ሰልፎች ምክንያት የሚከሰተው የሰዎች ህይወት መጥፋት በእጅጉ እንደሚያሳስበው እየገለፀ የፀጥታ ሀይሎች ተመጣጣኝ ያልሆነ ሀይል ከመጠቀም እንዲቆጠቡ ጥሪውን ያቀርባል፡፡

በክልሉ የተለያዩ ቦታዎች በተለይም በአሳሳ፣ አሰቦት፣ አወዳይ፣ ባሌ ሮቤ፣ ጭሮ፣ ደንገጎ፣ ድሬ ጠያራ፣ ዶዶላ፣ ገለምሶ፣ ጊኒር፣ ሀሮማያ፣ ሂርና እና ሻሸመኔ የሞት ጉዳት መድረሱን ኮሚሽኑ ከተለያዩ ምንጮች መረጃ ደርሶታል፡፡

የሞት ጉዳቶቹ የደረሱት የኦሮሞ ተቃዋሚ ፓርቲ ፖለቲከኞች እንዲለቀቁ በተጠሩ የተቃውሞ ሰልፎች እንደሆነም ለማወቅ ተችሏል፡፡

‹‹የመንግስት አካላት የዜጎችን በሰላማዊ መልኩ ተቃውሞ የማሰማት መብት ማረጋገጥ እንዳለባቸው እና ሕግ የማስከበር ስራ ተመጣጣኝነት እንዲጠብቅ ማድረግ እንደሚጠበቅባቸው›› የኮሚሽኑ ከፍተኛ አማካሪ እና ቃል አቀባይ አቶ አሮን ማሾ ገልፀዋል፡፡

‹‹የኦሮሚያ ክልል በዚህ አመት የተከሰቱ አሳዛኝ ግድያዎች ከፈጠሩት ሰቆቃ አሁንም ፈጽሞ አላገገመም፡፡ እነዚህ ከፍተኛ የመብት ጥሰት አዝማሚያዎች እንዲቀጥሉ ሊፈቀድላቸው አይገባም›› በማለት አክለው ገልጸዋል፡፡

እስካሁን በአንዳንድ ሚዲያዎች የወጡ ሪፖርቶች እና በማህበራዊ ሚዲያ የተለቀቁ መረጃዎች የሞቱ ሰዎችን ቁጥር በሚመለከት የተለያየ አሀዝ አስቀምጠዋል፡፡

ኢሰመኮ የደረሰውን ሞትና ጉዳት መጠን ለማረጋገጥ ከየአካባቢው ነዋሪዎች፣ ምስክሮች፣ ሆስፒታሎች እና የአስተዳደር አካላት መረጃ በማሰባሰብ ላይ ይገኛል፡፡

ኢሰመኮ የፌዴራል እና የክልል መንግስታት ጉዳዩን ለማጣራት በአፋጣኝ ምርመራ እንዲጀምሩ ጥሪውን ያቀርባል፡፡

አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 14 ቀን 2012 ዓ.ም.


1 min read

Published



Share this with family and friends


Follow SBS Amharic

Download our apps

Watch on SBS

SBS World News

Take a global view with Australia's most comprehensive world news service

Watch now