ለሕዳሴ ግድብ ግንባታ በኮንትራት መልኩ ተበጅቶ የነበረው ጠቅላላ በጀት 78.3 ቢሊዮን ብር ቢሆንም የግንባታው ሂደት ግና እስካሁን 120 ቢሊዮን ብር መፍጀቱን የሕዳሴ ግድብ ፕሮጄክት ዋና ሥራ አስኪያጅ ኢንጅነር ክፍሌ ሆሮ አስታውቀዋል።
አያይዘውም፤ የግድቡን ግንባታ ለማጠናቀቅ 160 ቢሊዮን ብር እንደሚፈጅ አመላክተዋል።
የፕሮጄክቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ ይህን የገለጡት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ በዛሬው ዕለት ከሕዳሴው ግድብ የቦርድ አመራሮችና አግባብ ካላቸው የፌዴራል መንግሥቱ ከፍተኛ አመራሮች ጋር ውይይት ባደረጉበት ወቅት ነው።
በውይይቱ ወቅት የግድቡ አጠቃላይ ግንባታ 78 በመቶ መድረሱን፤ የአሌሌክትሮ ሜካኒካል ሥራው 46.5 በመቶ እንዲሁም የሲቪል ክንዋኔው 88.8 በመቶ መድረሱ ተገልጧል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ የግድብ ግንባታውን ዳር የመድረስ እሳቤ አስመልክተው የተያዘውን በውል ውጥን ግብር ላይ ማዋል ከተቻለ በ2015 ግድቡ ለምረቃ እንደሚበቃና አስፈላጊው ሙሉ ድጋፍና ክትትል ተደርጎለት ነሐሴ 2013 ላይ 18.4 ቢሊዮን ኪዩቢክ ሜትር ውኃ መያዝ እንደሚችል ተናግረዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ "ታላቁ የህዳሴ ግድብ የነፃነት አርማችን ነው" ሲሉም የግድቡን አገራዊ ተምሳሌነት ሉዓላዊ ግዘፍ አላብሰው ገልጠዋል።