የኢትዮጵያ መንግሥትና የዓለም ምግብ ፕሮግራም በሕወሓት ጥቃቶች የተነሳ በአማራ እና በአፋር ክልሎች ለተፈናቀሉ ከ300 ሺህ በላይ ሰዎች የሰብዓዊ ዕርዳታ እያቀረቡ መሆኑን የጠቅላይ ሚኒስትር ጽ/ቤት ትናንት በወቅታዊ ጉዳዮች ዙሪያ ለጋዜጠኞች በሰጠው መግለጫ አስታወቀ፡፡
የጽህፈት ቤቱ ፕሬስ ሴክሬተሪያት የውጭ ቋንቋዎች እና ዲጂታል ሚዲያ ኃላፊ ቢልለኔ ስዩም እንዳሉት እስከ ነሐሴ 13 ቀን 2013 ዓ.ም ድረስ 318 የሰብዓዊ እርዳታዎችን የጫኑ ተሽከርካሪዎች መቀሌ ደርሰዋል፤ በሕወሓት ጥቃቶች የተነሳ ከአማራና ከአፋር ክልሎች ለተፈናቀሉ ከ300 ሺህ በላይ ሰዎች የኢትዮጵያ መንግሥት እና የዓለም ምግብ ፕሮግራም (WFP) ሰብዓዊ ዕርዳታ እያቀረቡ መሆኑንም ገልጸዋል፡፡

Humanitarian Aid. Source: Getty
በአማራ እና በአፋር ክልሎች ሕዝብ እያሸበረ፤ የሕክምና ተቋማትን ጨምሮ የግለሰቦችን ሀብትና ንብረት እየዘረፈ፤ የመሰረተ ልማት አውታሮችን እያወደመ፣ በወረራ በገባባቸው ንጹሃንን እያሰቃየና እየገደለ ነው ሲሉ የተናገሩት ቢልለኔ ሕወሓት ትናንትና በደብረ ታቦር ከተማ በተኮሳቸው ከባድ መሳሪያዎች ንጹሃንን ገድሏል ብለዋል፡፡
"ሕወሓት ለኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን ለአፍሪካ ቀንድ በአጠቃላይ የሰላም እና ጸጥታ ችግር ነው፤ ስለሆነም ሁሉም ዓለም አቀፍ የኢትዮጵያ ወዳጆች የሽብር ቡድኑ በአፍሪካ ቀንድ ካሉ ዓለም አቀፍ የሽብር ቡድኖች ጋር እያደረገ ያለውን ትብብር በጥንቃቄ ሊመለከቱትና ሊያወግዙት ይገባል” ሲሉም አክለዋል፡
ቢልለኔ በመግለጫቸው የጠቅላይ ሚኒስትሩ የቱርክ ጉብኝት በትብብር ስምምነቶች የተቋጨ፣ የአቀባበል ድምቀት የነበረውና የተሳካ እንደነበርም አውስተዋል፡፡

Press Secretary for the Office of the PMO Ethiopia Billene Seyoum Woldeyes speaks to press regarding the current issues in Tigray, in Addis Ababa, on August 13. Source: Getty
( ደመቀ ከበደ - አዲስ አበባ)