ጆ ባይደን ለዩናይትድ ስቴትስ 46ኛው ተመራጭ ፕሬዚደንት ከሆኑ በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ ባደረጉት ንግግር እሳቸውን ደግፈውም ይሁን ተፃርረው ለመረጡ አሜሪካውያን ሁሉ ደከመኝ ሰለቸኝ ሳይሉ ታትረው እንደሚሰሩ ተናግረዋል።
"ጊዜው የከረሩ አባባሎችን መክሊያ፣ ግለትን ማብረጃ፣ አንዳችን ካንዳችን ጋር መተያያና አንዳችን አንዳችንን ማድመጫና ወደፊት መራመጃ ነው፤ ተቀናቃኛችንን በጠላትነት መመሰሉን ማቆም አለብን" ብለዋል።
አቶ ባይደን በንግግራቸው ወቅት ዶናልድ ትራምፕን ስም አልጠቀሱም። ቅድሚያ ከሚሰጧቸው ዋነኛ አጀንዳዎቻቸው ውስጥ ኮቨድ - 19ን በቁጥጥር ስር ማዋል፣ የምጣኔ ሃብት እንዲያንሰራራ ማድረግ፣ ለዘር መድልዖ ፍትሕ ማስገኘትና የአየር ንብረት ለውጥን መከላከል እንደሆነ ጠቁመዋል።
አብረዋቸው ለምክትል ፕሬዚደንትነት ለድል የበቁትን ካማላ ሃሪሰን "የመጀመሪያ ጥቁር ሴት፣ ከደቡብ እስያ ዝርያ የመጀመሪያዋ ሴት፣ በአገራችን ታሪክ የመጀመሪያዋ ሴት ተመራጭ" በማለት ስኬታቸው ታሪካዊ መሆኑን ተናግረዋል።
ካማላ ሃሪስም በበኩላቸው "ለዚህ ቢሮ የመጀመሪያዋ ሴት ብሆንም፤ የመጨረሻዋ ግን አልሆንም" ብለዋል።

Vice President-elect Kamala Harris. Source: AFP
ጆ ባይደን 46ኛው የዩናይትድ ስቴትስ ፕሬዚደንት በመሆን ከተመራጭ ምክትል ፕሬዚደንት ካማላ ሃሪስ ጋር ጃንዋሪ 20 ቃለ መሃላ በመፈጸም ፕሬዚደንታዊ ስልጣን ተረክበው ኃላፊነታቸውን መወጣት ይጀምራሉ።