የ 2013 ምርጫ ዝግጅት ሂደትን ወቅታዊ ሁኔታ በተመለከተ የኢትዮጰያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ዛሬ በአዲስ አበባ ከፓርቲዎች ጋር መክሯል።
በተለይ በመራጮች ምዝገባ መረጃ፣ በምርጫ ቁሳቁስ ስርጭትና በፓርቲዎች እያጋጠሟቸው ባሉ ችግሮችና ተያያዥ ጉዳዮች ዙሪያ ለግማሽ ቀን ውይይት ተካሂዷል።
የምርጫ ቁሳቁስ ማጓጓዣ ችግር አፋጣኝ እልባት ካላገኘ አገር አቀፉን የምርጫ ሂደት ሊያስተጓጉል ይችላል ሲል የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ባቀረበው ሪፖርት ገልጿል።
የቦርዱ ሰብሳቢ ወይዘሪት ብርቱካን ሚደቅሳ የመንገድ መሰረት ልማት ውስንነት ያለበት አገር ላይ ምርጫን በአግባቡ ለማካሄድ መንግስት ከፍተኛ እገዛ ሊያደርግ ይገባል ብለዋል።
ሁሉንም የአገሪቱ አካባቢ ሊሸፍን የሚችል የትራንስፖርት አቅም ያለው መከላከያ ሰራዊት ነው ያሉት ሰብሳቢዋ በትግራይ በተፈጠረው ወቅታዊ ሁኔታ የተነሳ እገዛው መስተጓጎሉን ተናግረዋል።
ክልሎች በልዩ ትኩረት ካልተባበሩና ያለው የማጓጓዣ ችግር አፋጣኝ እልባት ካልተሰጠው የምርጫ ሂደቱን በከፍተኛ ሁኔታ ሊያስተጓጉል ይችላል ብለዋል ወይዘሪት ብርቱካን። በየደረጃው ያሉ የክልል አመራሮች የመጓጓዣ ችግሩን ለመፍታት ከቦርዱ ጋር መተባበር እንዳለባቸው ነው ያሳሰቡት።
ምርጫ ቦርድ በመላ አገሪቷ 663 የምርጫ ክልሎችን ከፍቶ የምርጫ ቁሳቁሶችን እያጓጓዘ ሲሆን በቀጣይ ለ50 ሺህ ምርጫ ጣቢያዎች እንደሚያሰራጭ አስታውቋል። ማጓጓዣው በየአካባቢው እንዳለው መሰረተ ልማት በየብስ ፣ በጀልባ እንዲሁም በበቅሎና ፈረስ ጭምር ሊሆን እንደሚችል ነው ያመለከቱት።
በዛሬው ምክክር ወቅት ከተነሱ ጉዳዮች አንዱ የነበረው የምርጫ ጣቢያዎች መከፈትና ስራ መጀመርን የተመለከተው አንዱ ነበር። በተለይ የመተከል ጉዳይ። ቦርዱ እንዳስታወቀው በመተከል ዞን በሁሉም ወረዳዎች የምርጫ ጣቢያዎች መከፈታቸውን ገልጿል።
ቦርዱ በመተከል ዞን በሚገኙት 7 ወረዳዎች የምርጫ ጣቢያ መከፈቱን የገለፀ ሲሆን በስድስት ክልሎችም የእጩ ምዝገባ መጀመሩን ወይዘሪት ብርቱካን አስረድተዋል። ድሬደዋ፣ አዲስ አበባ ፣ ኦሮሚያ፣ ጋምቤላ፣ ሃረሪ እና ቤኒሻንጉል ጉሙዝ ሲሆኑ በተቀሩት ክልሎች ደግሞ ከዛሬ ጀምሮ የእጩ ምዝገባ ሂደቱን ይጀምራሉ ብለዋል፡፡
በውይይቱ የፓርቲ ተወካዮች ያሉባቸውን ችግሮችና በገዥው ፓርቲ በኩል እያጋጠሟቸው ያሉ እንቅፋቶችን ያነሱ ሲሆን ቦርዱ አስፈላጊውን ድጋፍና ክትትል እንዲያደርግም ጠይቀዋል።
[ ደመቀ ከበደ ፡ አዲስ አበባ ]