የዩናይትድ ስቴትስ ፕሬዚደንታዊ ምርጫ እስካሁንም ብርቱ ፉክክር ቢታይበትም ለፕሬዚደንትን የሚያበቃውን 270 የምርጫ ኮሌጅ ድምፅ ለማግኝት የዲሞክራቱ ዕጩ ፕሬዚደንት ጆ ባይደን በእጅጉ ተቃርበዋል።
ጆ ባይደንም ለዩናይትድ ስቴትስ ፕሬዚደንትነት የሚያበቃውን የምርጫ ኮሌጅ አስፈላጊ ቁጥር እንደሚያገኙ ያላቸውን አመኔታ ገልጠዋል።
ከፕሬዚደንት ትራምፕ ጋር የጠበቀ ወዳጅነት ያለው ፎክስ ኒውስ ጆ ባይደን 264 - ዶናልድ ትራምፕ 214 የምርጫ ኮሌጅ ድምፅ እንዳገኙ ሲያመለክት፤ CNN እና ኒው ዮርክ ታይምስ ጆ ባይደን 253 - ዶናልድ ትራምፕ 214 የምርጫ ኮሌጅ ድምፅ እንዳገኙ ሪፖርት አድርገዋል።
ጆ ባይደን አሪዞናና ኔቫዳ ላይ ዶናልድ ትራምፕ ፔንሲልቫኒያ ላይ በመጠነኛ ድምፅ እየተመራሩ ይገኛሉ።
ጆ ባይደን ከጥቂት ሰዓታት በፊት ቀጣዩ የዩናይትድ ስቴትስ ፕሬዚደንት ሆነው እንደሚመረጡ በመተማመን ሲናገሩ፤
"ከረጅም ምሽት ቆጠራ በኋላ አሁን ለፕሬዚደንታዊ ድል ለመብቃት የሚያስችለንን 270 ድምፆች ለማግኘት በቂ ድምፆች ያሉን መሆኑ ግልጽ ነው። እዚህ አሁን የተገኘሁት ድል ለማብሰር አይደለም፤ ይሁንና ቆጠራው ሲያበቃ ግና አሸናፊዎች እንደምንሆን እናምናለን" ብለዋል።
ፕሬዚደንት ትራምፕ በበኩላቸው ምንም እንኳ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ የምርጫ ድምፆች ገና ቆጠራ ላይ ያሉ ቢሆንም ትናንት ማምሻውን በሰጡት መግለጫ ራሳቸውን ባሸናፊነት ሰይመዋል። የምርጫው ሂደትም ማጭበርበር እንዳለበትና ቆጠራውም እንዲያበቃ ወደ ዩናይትድ ስቴትስ ጠቅላይ ፍርድ ቤት አቤት ለማለት እንደሚያመሩ ተናግረዋል። በተወሰኑ የምርጫ ጣቢያዎችም ዳግም ቆጠራ እንዲካሄድ ጠይቀዋል።