አንኳሮች
- ውልደትና ዕድገት
- ትምህርትና ሥራ
- የባህር ማዶ ሕይወት
ውልደትና ዕድገት
ማርታ አበጋዝ ገብሬ፤ የሁለት እህቶቿና አንድ ወንድሟ ተከታይ ሆና ለቤተሰቧ አራተኛ ልጅ ናት።

የማርታ ውልደትና ዕድገት ሳሪስ - አዲስ አበባ ነው።

ከአንደኛ ደረጃ እስከ ዩኒቨርሲቲ ትምህርቷን ያጠናቀቀችውም እዚያው በአገረ ኢትዮጵያ መዲና አዲስ አበባ ነው።
ምንም እንኳ በእጅጉ የትምህርት ደጋፊ ወንድሟ ምኞት ሐኪም ማርታን ማፍራት ቢሆንም፤ እንደ አባቷ ሁሉ ልብና አዕምሮዋ የዳዳው ግና የምሕንድስና ሙያን ነበር።
ትልሟ ሕልም ሆኖ አልቀረም፤ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የከፍተኛ ተቋም ትምህርቷን አጠናቅቃ በኮንስትራክሽን አስተዳደር በዲግሪ ተመረቀች።

ከምረቃ ወደ ሥራ
ማርታ አበጋዝ፤ የአምስት ዓመት የዩኒቨርሲቲ የኮንስትራክሽን አስተዳደር ትምህርቷን አጠናቀቀች። በሰለጠነችበት ሙያ ወደ ሥራው ዓለም ለመዝለቅ ተነሳች።
ሆኖም የሥራ ፍለጋ ሂደቱ በአደይ አበባ ስጋጃ ምንጣፍ የመረማመድ ያህል ሞገስን አላብሶ አፈር አይንካሽ ባይ አልሆነም።
ዩኒቨርሲቲ ሳለች "ኢትዮጵያ ውስጥ የምሕንድስና ሥራ ገና ያልተነካ የሙያ ዘርፍ ነው" ተብሎ ቢነገራትም፤ በገሃዱ ዓለም የጠበቃት ግና የመጀመሪያ ሥራዋን ለማግኘት የአንድ ዕንቁጣጣሽ ዕድሜ ማስቆጠርን ነው።
ሲልም አካውንታት "መሐንዲስ" ሆኖ ሲሠራ ለዓይን እማኝነት አብቅቷታል።
'እልፍ ሲሉ ዕልፍ ይገኛል' እንዲባል፤ የመጀመሪያ ሥራዋን በፈቃዷ ለቀቀች። ለአውስትራሊያ የሥራ ገበያ የበጃትን መልካም ልምድ ወደ ቀሰመችበት ሌላ ኩባንያ አመራች።
ሕይወት በሥራ ዓለም ብቻ አይወሰንምና ከተዋወቅችው አምስት ዓመት ያህል ካስቆጠረችው የአውስትራሊያ ነዋሪ ጋር በፍቅር ወደቁ።
ኢንጂነር ማርታ አበጋዝ ገብሬ እና መዝሙር አቸነፈ ዓለሙ ለቤተ ክርስቲያን ሥርዓተ ጋብቻ በቁ።

የማርታና መዝሙር "እህል ውኃ" ለእገረ አውስትራሊያ ታደለ።
ኢትዮጵያ ውስጥ በሙሉ ልብ በምሕንድስና ሙያ በምረቃዋ ማግሥት አገኛለሁ ብላ ተማምና የነበረችው ማርታ ለአንድ ዓመት ሥራ ፈላጊነት ግድ የመሰኘቷ ተሞክሮ፤ አውስትራሊያ ውስጥ በሙያዋ ተሠማርታ የመሥራት ዕድሏ ላይ ብርቱ ጥርጣሬ አሳደረባት።
ሆኖም ጥርጣሬዋ የተገላቢጦሽ ሆነ። የአውስትራሊያን ምድር በረገጠች በሁለት ወሯ በኮንስትራክስሽን ኢንዱስትሪ በግንባር ቀደምትነት ከሚነሱት አንዱ በሆነው ግዙፉ ጆን ሆላንድ ኩባንያ በተገዲብ መሐንዲስነት ሥራ ለመሠማራት በቃች።
አሁንም ድረስ እየሠራች ያለችው እዚያው ነው።

ከነገ ጋር ቀጠሮ
ኢንጂነር ማርታ አበጋዝ ቀሪ ሕይወቷን ለመምራት የምትሻው በሙያዋ ዘርፍ አድጋ ከፍተኛ ደረጃ ላይ ለመድረስና ከባለቤቷ መዝሙር አቸነፈ ጋር በጣም ደስተኛ ቤተሰብ መሥርቶ መኖርን ነው።

"እግዚአብሔር የባረከው ባለቤት ነው ያለኝ"ኢንጂነር ማርታ አበጋዝ





