የመሪነት ዕሳቤ ውስጣቸው የሰረጸው ገና ለጋ ወጣት ሳሉ ነው።የዘጠነኛ ክፍል ተማሪ ሆነው የተማሪዎች ማኅበር አቁመው የመጀመሪያዋ ፕሬዚደንት ሆነዋል።
“መሪነት በችሮታ አይሰጥም፤ የሚወሰድ ነው።” ብለው ያምናሉ።
“መሪነት በችሮታ አይሰጥም፤ የሚወሰድ ነው።”
የልጅነት ሕልማቸው የአመራር ወንበራቸውን ፒያሳ ህንፃ ላይ ማድረግ ነበር። የፒያሳ ሰማይ ጠቀስ ህንፃ ከሰሞነኛ ርዕሰ ዜናነት ሳያልፍ ቀረና ያ አልሆነም።
ግና ብዙም ሳይርቁ፤ ትንሽ ፈንጠር ብለው የመጀመሪያዋ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የሴት ምክትል ከንቲባ ሆነዋል። ቀን ቆርጠን የተነጋገርነውም እዚያው የማዘጋጃ ቤቱ ቢሮአቸው ውስጥ ነው።
የረፋዷ የአገር ቤት ጸሐይ ለቢሮአቸው ያለስስት ብርሃኗን ለግሳ ድምቀትን አላብሳላቸዋለች። የግድግዳው ክሪም ቀለም በጥንቃቄ ከተመረጠው የስጋጃ ምንጣፍና አገርኛ ትንቡኬ መቀመጫ ጋር ተስማምተው ክፍሉን ሞገስ አላብሰውታል። ጥጋቱ ላይ ዘለግ ብለው የወጡትና የጽህፈት ጠረጴዛቸው ፊት ለፊት ተዛንቀው የተቀመጡት ባለ ሕብረ ቀለማት አበቦች ተሰናስለው ቢሮውና ወንበሩ በእንስት የተያዙ መሆኑን ይመሰክራሉ። ውስጣዊ ስክነትን ያላብሳሉ።
ዳግማዊትም ነቃና ዘና እንዳሉ ነበር ስለ SBS የምስረታ ታሪክና አስተዋጽዖዎች፣ ዲሞክራሲ በአገረ አውስትራሊያ በግብር ላይ እንደምን እየዋለ እንዳለ አዋዝተን፤ የሐዋሳውን የኢሕአዴግ 11ኛ መደበኛ ጉባኤ በቅንጭቡ ነቅሰን፤ የኢትዮጵያውያን ሴቶችን የፖለቲካ ተሳትፎ በእሳቸው ሕይወት ዙሪያ ቃኝተን ወደ ቃለ ምልልሳችን የገባነው።

Dagmawit Moges Source: SBS Amharic

Addis Ababa City Hall Source: SBS Amharic

Dagmawit Moges Source: SBS Amharic

Dagmawit Moges and Kassahun Seboqa Source: SBS Amharic





