እንደወጡ አልቀሩም፤ ከ፲፩ ዓመታት የግብጽና ጀርመን የአፍላ ወጣትነት የትምህርት ጥማት እርካታ በኋላ ወደ አገራቸው ኢትዮጵያ ተመልሰዋል።

ሕልማቸው የባህር ማዶ ዕውቀትን በመምህርነት ለአገር ዕድገት ማዋል ነበርና ቀድመው ያመሩት ወደ ትምህርት ሚኒስቴር ነበር። ወቅታዊ ምላሽ ሳያገኙ ቀሩ። ተስፋ አልቆረጡም። ይልቁንም የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚደንት የነበሩት የዶ/ር አክሊሉ ኃብቴን ቢሮ በር አንኳኩ። ፕሬዚደንቱ በአንድ እጃቸው በራቸውን ገርበብ አድርገው ከፍተው በሌላ እጃቸው ወደ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መንገድ አመላከቷቸው።
እንደተባሉት ወደ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አቀኑ። ሚኒስትር ከተማ ይፍሩን አነጋገሩ። አቶ ከተማም የመካከለኛው ምስራቅ ጉዳይ የሚከውንላቸው የተማረ ሰው ይፈልጉ ነበርና ‘ለምን አታግዘኝም?’ ብለው ጠየቁ።
የዶ/ር ጌታቸው ምላሽ እሺታ ሆነ። ክረምቱን በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ሠራተኛነት አሳለፉ። ክረምቱ በበጋ ሲተካ፤ በዶ/ር አክሊሉ ኃብቴ በኩል የኢትዮጵያ ቋንቋዎችና ጥናት ክፍል አስተማሪ እንደሚፈልግ ተጠቆሙ።
ውስጣቸው ተቀብሮ የነበረው የአስተማሪነት መንፈስ ገንፍሎ ወጣ። የልጅነት ምኞታቸውን ዕውን ለማድረግ ውጭ ጉዳይን ጥለው ወደ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ እብስ አሉ። መንበራቸውን ዘርግተው ማስተማር ጀመሩ።
በአስተማሪነቱ ጥቂት ጊዜያትን እንደገፉ በድንገት ከግቢ ጥሪ ደርሳቸው። ንጉሠ ነገሥቱ ዘንድ ቀረቡ። በቤተክህነት አስተዳዳሪነት መሾማቸው ተነገራቸው። ቅሬታቸውን በልባቸው ይዘው እጅ ነስተው ወጡ።

ከግቢ እንደወጡ ገስግሰው የሄዱት ወደ ዩኒቨርሲቲው ፕሬዚደንት ዘንድ ነበር። ከመምህርነት ወደ አስተዳዳሪነት እንደምን ሊሾሙ እንደበቁ ለመጠየቅ። የተሰጣቸው ምላሽ ግና አላረካቸውም።
እናም፤ የሌላ ቅሬታ ሰሚ በር ማንኳኳት ግድ ሆነ። ለሹመት ያቀረቧቸው ጠቅላይ ሚኒስትር ፊት ቀረቡ። ብቃትና ውዴታቸው ማስተማር እንጂ ማስተዳደር አለመሆኑን አዋዝተው ተናገሩ። ጠቅላይ ሚኒስትሩም ተዋዝቶ የቀረበው ቅሬታ ገብቷቸው ከሳቅ ጋር በብቃትና ውዴታቸው እንዲሰሩ ለማድረግ ጥረት እንደሚያደርጉ ቃል ሰጥተው ሸኟቸው። የጠቅላይ ሚኒስትሩ ቃል በግብር ዋለ።





