ዶ/ር አበራ ሞላ፤ ዘርፈ ብዙ በሆኑ የምርምርና ፈጠራ መስኮች ስመጥር ተጠባቢ ናቸው። በእንሰሳት ሕክምና ዘርፍ የመድን ማነስን በማስወገዱ ረገድ ከዓለም አቀፍ ሳይንቲስቶች የመጀመርያው ተርታ ተሠልፈዋል። የግዕዝ ፊደል ተጠቃሚዎችንም በዘመናዊው ኮምፒዩተርና የእጅ ጮሌ ስልኮቻቸው እንዲተይቡ ያስቻሉ የፈጠራ ሰው ናቸው። በቀዳሚው ክፍል አንድ ውይይታችን የግለ ሕይወት ታሪካቸውን ቀንጭበው መተረክ የሚጀምሩት ከትውልድና ዕድገት ሥፍራቸው ነው።
ውልደታቸው ሰንዳፋ፤ ኢትዮጵያ ነው። ለመጀመሪያ ጊዜ ፊደል የቆጠሩት እንደ አያሌ ኢትዮጵያውያውያን ቄስ ትምህርት ገብተው ሳይሆን በቀጥታ አስኳላ ዘልቀው ነው።
በቀለሙ ገፍተው የሁለተኛ ደረጃ ትምህርታቸውን አጠናቅቀዋል። ኮሌጅ በጥሰዋል። በዚያም አልተገቱም፤ ለድኅረ ዶክትሬት ኮሎራዶ ስቴት ዩኒቨርሲቲን ረግጠው እ.ኤ.አ. በ1975 በእንሰሳት ሕክምና ተጠብበዋል።

በምርምር ግኝታቸው የመድኅን ማነስን (immune deficiency) ለመክላት በመብቃታቸው በሚሊየን የሚቆጥሩ የእንሰሳት ህይወቶችን ታድገዋል። በቢሊየን ዶላርስ የሚቆጠሩ ወጪዎችን አድነዋል።

በኤች.አይ.ቪ ኤይድስ ምርምር መስክ ከዓለም አቀፍ ሳይንቲስቶች ጋር ተሰማርተው መከላከያውን ለማግኘት ብርቱ ጥረቶችን አከናውነዋል።
ጥሬ ሥጋ መመገብን ልማዳቸው ላደረጉቱና በዓል በመጣ ቁጥር በድብቅ በየእርሻ ማሳው ዘልቀው ሙክትና ድልብ ሰንጋ ለሚያሳርዱቱ፤ ከጤናና ከሕግ አኳያ ምክረ ኃሳቦቻቸውን ያጋራሉ።
“ጥሬ ሥጋ መብላት እንደ ቁማር ነው፤ ሁሌም አያዋጣም። ኃይለኛ በሽታ የተገኘ ቀን ብዙ ሰው ሊያልቅ ይችላል።” - ዶ/ር አበራ ሞላ Image “ብዙዎች ኢትዮጵያውያን በየእርሻው እየሔዱ ያንን በግ፤ ያንን ከብት እረድልኝ ሲሉ ከሸጠላቸው ሰው ኃላፊነቱን መውሰዳቸውን አይረዱም። ያን ሥጋ ሰው በልቶ ቢሞት፤ ኃላፊነቱ ያሳረደው ወይም የገዛው ሰው ነው።” - ዶ/ር አበራ ሞላ






