አውስትራሊያ - ቻይና የንግድ ውዝግብ
የአውስትራሊያ ንግድ ሚኒስትር ሳይመን በርሚንግሃም እያደገ የመጣውን የንግድ ውጥረት ለማርገብ ከቻይናው አቻቸው ጋር በስልክ ለመነጋገር ቢጥሩም እንዳልተሳካላቸው ገልጡ።
አውስትራሊያ የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝን መነሻ አስመልክቶ ምርመራ እንዲካሄድ እየገፋች ባለችው አጀንዳ ቁጣን የተላበሰችው ቻይና፤ በአራት የእርድ ከብት ሥጋ አቅራቢ ድርጅቶች ላይ ዕገዳንና በገብስ የውጭ አቅርቦት ምርት ላይ ታሪፍ ጥላለች።
ይሁንና ሴናተር በርሚንግሃም የቻይና ዕገዳና ታሪፍ ከኮቪድ - 19 ምርመራው ጋር ተያያዥነት የለውም ባይ ናቸው።
ሚኒስትሩ ምላሽ ባያገኙም ጥረታቸው እንደሚቀጥል ሲገልጡ፤
" ከቻይናው አቻዬ ጋር ለመወያየት እንድችል ጥያቄ አቅርበናል። እስካሁን ጥያቄያችን ምላሽ አላገኘም። የአውስትራሊያ መንግሥት የአቋም ልዩነት ያላቸውን ጨምሮ ከዓለም አቀፍ ሽርካዎቹ ጋር ማስተዋል የተመላመበትና ማለፊያ ውይይት ለማድረግ ሁሌም በሩ ክፍት መሆኑን ገልጫለሁ። በአፀፋው የሁለትዮሽ ተግባቦቶችን ለማካሔድ ወይም ላለማካሔድ መወሰን ግና የእነሱ ፈንታ ነው" ብለዋል።
አክለውም፤ ምናልባትም ቻይና በዛቻዋና እርምጃዋ ከቀጠለች አውስትራሊያ ክሷን ወደ ዓለም የንግድ ድርጅት ልትወስድ እንደምትችል አሳስበዋል።
ቻይና የአውስትራሊያ አንድ ቁጥር የንግድ ሽርካ ብትሆንም፤ ሴናተር በርሚንግሃም 'የንግድ ተቋማት ሸቀጦቻቸውንና ግልጋሎቶቻቸውን ለማን መሸጥ እንዳለባቸው መወሰን የነሱ ፈንታ ነው' ብለዋል።
ቫይረስ - ቪክቶሪያ
የቪክቶሪያ መንግሥት በኮሮናቫይረስ ሳቢያ ተጥለው የነበሩትን ገደቦች ለማላላት በወጠነው ዕቅድ መሠረት ከጁላይ 1 ጀምሮ ምግብ ቤቶች፣ ካፌዎችና መጠጥ ቤቶች ክፍት ይደረጋሉ።
ማስተናገድ የሚችሉትም እስከ 20 ሰዎች ይሆናል።
በጁላይ አጋማሽ ላይም ትላልቅ አዳራሾች ያሏቸው እስከ 100 ደምበኞችን ማስተናገድ ይችላሉ።
ቫይረስ ምዕራብ አውስትራሊያ
የምዕራብ አውስትራሊያ ፕሪሚየር ማርክ ማክጋዋን ከሰኞ ጀምሮ ምግብ ቤቶች፣ ካፌዎችና መጠጥ ቤቶች ዳግም ሲከፈቱ ነዋሪዎች ድጋፍ እንዲያደርጉላቸው አሳሰቡ።
ግልጋሎት ሰጪዎቹ ከነገ ጀምሮ በአንድ ጊዜ እስከ 20 ደምበኞችን እንዲያስተናግዱ ተፈቅዶላቸዋል።
የቪክቶሪያው ፕሪሚየር ዳንኤል አንድሩስና ማክጋዋን ነዋሪዎቻቸው ማኅበራዊ ርቀትን ከመጠበቅ እንዳይዘናጉ አሳስበዋል።

