የቦርዱ ሰብሳቢ ወ/ሮ ሜላትወርቅ ኃይሉ ትናንት ማምሻውን በሰጡት መግለጫ፣ በኦሮሚያ ክልል በሚገኙት ቢሎኖጳ፣ መኮሳቺ እና ቀርሳ የምርጫ ክልሎች የጸጥታ ሁኔታው መሻሻል ባለማሳየቱ ምርጫው ሊካሄድ እንዳልቻለ ገልጸዋል።
ሰብሳቢዋ እንደተናገሩት፣ በቢሎኖጳ የነበረው የጸጥታ ችግር ምርጫው በታቀደበት ጊዜ እንዳይካሄድ ያደረገ ሲሆን፣ ቦርዱ ሂደቱ በሚቀጥለው ቀን እንዲካሄድ ውሳኔ ማሳለፉን አስታውቀዋል። በመኮሳቺ ግን የፀጥታ ችግሩ ቀጥሎ በመቆየቱ የድምፅ መስጠት ሂደት እንዳልተካሄደ ገልጸዋል።
በአማራ ክልል በሚገኘው የኩታበር ምርጫ ክልልም በጸጥታ ችግር ምክንያት የተቋረጠው ሂደት በከፊል ወደ መደበኛ ሁኔታ መመለሱን ገልጸዋል።
ከ19 የምርጫ ጣቢያዎች ውስጥ በ15ቱ ድምፅ መስጠት እንዲካሄድ የሚያስችል ሁኔታ መፈጠሩን ሲገልጹ፣ ቀሪዎቹ 4 ጣቢያዎች ግን አሁንም ምርጫ ሳይካሄድባቸው መቅረታቸውን አስታውቀዋል።
በተቋረጡት የምርጫ ጣቢያዎች ምን ዓይነት ጉዳት እንደደረሰ በተጠየቁበት ወቅት ወ/ሮ ሜላትወርቅ፣ የደረሰው ጉዳት በዝርዝር እየተጣራ መሆኑን ገልጸዋል።
“የተፈጠረውና የደረሰው ጉዳት በዝርዝር የሚጣራ ነው። ተቃጥሏል ወይስ ወድሟል? የደረሰው ጉዳት ምን ያህል ነው? ምን ዓይነት ክስተት ተፈጥሯል? የሚለው በሙሉ መጣራት ይጠይቃል። ማጣራቱ ሳይጠናቀቅ በዚህ ደረጃ ዝርዝር መረጃ መስጠት አይቻልም፤ ሙሉ ማጣራት ከተደረገ በኋላ ቦርዱ ይፋዊ ምላሽ ይሰጣል” ብለዋል።
የምርጫ ቦርዱ በተቋረጡት ጣቢያዎች ላይ የደረሰውን ጉዳትና የፀጥታ ክስተቶችን በዝርዝር እየመረመረ መሆኑን ገልጾ፣ የማጣራት ሂደቱ ከተጠናቀቀ በኋላ ተጨማሪ መረጃዎችን ለሕዝብ እንደሚያቀርብ አስታውቋል።

