የዩናይትድ ስቴትስ ልዩ ልዑክ ጄፍሪ ፌልትማን ዛሬ ከኬንያ ወደ ኢትዮጵያ ዳግም ተመልሰዋል።
ልዩ ልዑኩ ከኖቬምበር 4 - 7 ከጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ፣ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን፣ የመከላከያ ሚኒስትር አብርሃም በላይና የገነዘብ ሚኒስትር አሕመድ ሺዴ ጋር ተገናኝተው የሰሜን ኢትዮጵያ ወታደራዊ ግጭትን አስመልክተው ተወያይተዋል።
በተጓዳኝም ከአፍሪካ ኅብረት ከፍተኛ የምሥራቅ አፍሪካ ተወካይ ኦሉሴጉን ኦባሳንጆ፣ የአፍሪካ ኅብረት ኮሚሽን ሊቀመንበር ፋኪ ማሃማት፣ የተመድ ተወካይ ማርቲን ግሪፊዝና ከሌሎች ዓለም አቀፍ ሽርካዎችና የመንግሥታት መሪዎች ጋርም መክረዋል።
አቶ ፌልትማን ከኖቬምበር 7 - 8 ከኬንያው ፕሬዚደንት ኡሁሩ ኬንያታና የፖለቲካ መሪዎች የሰሜን ኢትዮጵያ ወታደራዊ ግጭት የሚፈታበትን ብልሃት ለማፈላለግ ምክረ ሃሳቦችን ተጋርተዋል።
በዛሬው ዕለትም ኦባሳንጆን ጨምሮ ዳግም አግባብ ካላቸው መሪዎችና ሽርካዎች ጋር በጉዳዩ ላይ ለመምከር ከናይሮቢ ወደ አዲስ አበባ ተመልሰዋል።
በሌላም በኩል ኖቬምበር 4 ወደ ኢትዮጵያ የዘለቁት ኖቬምበር 8 አዲስ አበባ ላይ በበይነ መረብ ለተካሔደው 1045ኛው የኅብረቱ የሰላምና ፀጥታ ምክር ቤት ስብሰባ እየተካሔደ ያለውን የሰሜን ኢትዮጵያን ግጭት አስመልክተው ባለ ስድስት ነጥብ ሪፖርታቸውን አቅርበዋል።
የቀድሞው የናይጄሪያ ፕሬዚደንት በሪፖርታቸው ውስጥ ለግጭቱ ዕልባት ለማበጀት ከኢትዮጵያ መንግሥትና የሕወሓት መሪዎች ጋር መወያየታቸውን አስረድተዋል።

የሰላምና ፀጥታ ምክር ቤቱም የኢትዮጵያ መንግሥትና ሕወሓት ያለ ምንም ቅድመ ሁኔታ ፖለቲካዊ ውይይት እንዲያካሂዱ በብርቱ እንዲያበረታታ፣ በሁሉም ተፋላሚ ወገኖች በኩል ያለ ምንም ቅድመ ሁኔታ የተኩስ አቁም እንዲካሄድ፣ የሰብዓዊ ረድኤት ተደራሽነት ያለ አንዳች ኧክል እንዲደርስ እንዲደረግ፣ በሁሉም ወገኖች ዘንድ ዓለም አቀፍ ሰብዓዊነትና የሰብዓዊ መብቶች ሕጎች እንዲያከብሩ፣ ሁሉንም አካታች የሆነ ብሔራዊ መግባባትና ዕርቅ እንዲካሔድና ዓለም አቀፍ ማኅበረስቡም ለምናካሂዳቸው የኅብረት ዓላማና የሰላም ጥረቶች ከአፍሪካ ኅብረት መራሹ ሂደት ጀርባ እንዲሰለፍ ጥሪ እንዲያቀርብ አሳስበዋል።
ኦባሳንጆ በአማራና አፋር ክልሎች ለመገኘት ወደዚያ አቅንተዋል።

