በሩስያና ዩክሬይን ልዑካን መካከል ቤላሩስ ላይ የተካሔደው የመጀመሪያ ዙር ንግግር ስኬታማ ሳይሆን አብቅቷል።
በዩክሬይን በኩል የቀረበው ጥያቄ አስቸኳይ ተኩስ አቁም እንዲደረግና የሩስያ ጦር ዩክሬይንን ለቅቅቆ እንዲወጣ ሲሆን በክሬምሊን በኩል ይፋ መግለጫ አልተሰጠም።
የልዑካን ቡድናቱ ለሁለተኛው ዙር ንግግር በሚበጁ ጉዳዮች ላይ ለመምከር ወደ መዲናዎቻቸው መስኮብና ኪየቭ ተመልሰዋል።
የ RIA ዜና እኤጀንሲ እንዳመለከተው ከሆነ የዩክሬይን ፕሬዚደንት አማካሪ ሚካኺሎ ፖዶልያክ ሩስያ ድርጊቷን "ልዩ ዘመቻ" ብላ የጠራችው የዩክሬይን ግዛት በአገዛዟ ስር ይዛ ለመቆየት ሳይሆን የዩክሬይንን ወታደራዊ አቅም ለማውደምና አደገኛ ብሔረተኞች ያለቻቸውን ጠልፎ ለመውሰድ እንደሆነ መናገራቸውን ገልጧል።
ይኼው የመጀመሪያ ዙር ንግግር እየተካሔደ ባለበት ወቅትም ዩክሬይን የአውሮፓ ኅብረት አባል አገር ለመሆን የአባልነት ማመልከቻ ቅጽ ሞልታ አስገብታለች።
የዩክሬይን ፕሬዚደንት ዜሌንስኪ የአውሮፓ ኅብረት ማመልከቻ ቅጽ ላይ ሲፈርሙ የተነሱትን ፎቶግራፍ በማኅበራዊ ገፃቸው ላይ አስፍረዋል። የዩክሬይን የአውሮፓ ኅብረት አባልነት ጥየቃ ሂደት ይሁንታን ለማግኘት ሁለት ዓመታትን የሚፈጅ ሲሆን አሁናዊ ፋይዳው ለሩስያው ፕሬዚደንት የዩክሬይንን እምቢተኝነት ለማሳየት የታሰበ ነው።
በሌላም በኩል፤ የተባበሩት መንግሥታት 193 አባል አገራት ጠቅላላ ጉባኤ ከአሠርት ዓመታት ወዲህ ለሩስያና ዩክሬይን ጦርነት ዕልባት ለማበጀት ለመጀመሪያ አስቸኳይ ስብሰባው ታድሟል።
ሁሉም የተመድ አባል አገራት በጉባኤው ላይ ጦርነቱን አስመልክቶ የየራሳቸውን አተያዮች የሚያቀርቡ ሲሆን፤ በሳምንቱ መገባደጃ ላይም በጉባእኤው ረቂቅ መግለጫ ላይ ድምፅ ይሰጡበታል።
ይህ በእንዲህ እንዳለም አውስትራሊያ ለዩክሬይን ወታደራዊና ሰብዓዊ እርዳታ የሚውል 105 ሚሊየን ዶላርስ መለገሷን ጠቅላይ ሚኒስትር ስኮት ሞሪሰን አስታወቁ።
አቶ ሞሪሰን በድጋሚ አውስትራሊያውያን ወደ ዩክሬይን ተጉዘው በጦርነቱ እንዳይሳተፉ ደግመው ከሕጋዊ መዘዞቹ ጋር አያይዘው በብርቱ አስጠንቅቀዋል።

