የዩናይትድ ስቴትስ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አንቶኒ ብሊንከን አምባሳደር ማይክል (ማይክ) ሐመር አዲሱ የአፍሪካ ቀንድ ልዩ ልዑክ ሆነው መሰየማቸውን አስታወቁ።
አምባሳደር ሐመር የየተኩት ኃላፊነታቸውን በለቀቁት የቀድሞው የአፍሪካ ቀንድ ልዩ ልዑክ አምባሳደር ዴቪድ ሳተርፊልድ ምትክ ነው።
የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ተሰናባቹን አምባሳደር ሳተርፊልድ በልምድ የካበተ ሚናና አስተዋፅዖ አንስተው በማመስገን ተተኪያቸው አምባሳደር ሐመር ዩናይትድ ስቴትስ በአፍሪካ ቀንድ ለምታደርጋቸው ጥረቶች ተጨማሪ ጉልበትና ርዕያቸውን እንደሚያክሉ ያላቸውን ተስፋ ገልጠዋል።

አክለውም ዩናይትድ ስቴትስ አዲሱ ልዑክ መመደብ ለቀጣናው ያላትን የማያመነታ ዲፕሎማሲያዊ ጥረቶችን የሚያመላክትና እንዲሁም በጣሙን መላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ለሚያሻውና ወደ ሰላም፣ የጋራ ደኅንነትና ብልፅግና ለሚያመራው አካታች ፖለቲካዊ ሂደት ድጋፍን ለመስጠት እንደሆነ አመላክተዋል።
የዩናይትድ ስቴትስ አስተዳደርም ግጭቶችን የመግታት፣ ያልተገደበ ሰብዓዊ ተደራሽነት፣ በሰብዓዊ መብቶች ጥሰቶች ላይ ግልፅ ምርመራዎችና በድርድር የግጭት መፍትሔ ላይ እንዲደረስ ብርቱ ትኩረት ከመስጠት ወደ ኋላ እንደማይልም አስታውቀዋል።
ማይክ ሐመር ቀደም ሲል በቺሊና ኮንጎ የዩናይትድ ስቴትስ አምባሳደር ሆነው አገልግለዋል።

