የአዲስ አድማስ ዝግጅት ክፍል፣ የጋዜጣው መሥራችና ዋና አዘጋጅ የነበረው ገጣሚና ደራሲ ነቢይ መኮንን ሕይወት ማለፉን ልጁ ራዕይ ነቢይ ገልጧል።
ከአዲስ አድማስ መሥራቾች አንዱ የሆነውና በዋና አዘጋጅነት ጋዜጣዋን በመምራት ተወዳጅ ካደረጓት በቀዳሚነት የሚጠቀሰው ነቢይ ብርቱ ተርጓሚ፣ ገጣሚና ወግ አዋቂ የጥበብ ሰው በመሆኑ ይታወቃል።

ነቢይ በደርግ ዘመን በእስር ላይ እያለ Gone with the wind የተሰኘውን የማርጋሬት ሚቼል መፅሀፍ በሲጋራ ወረቀት ላይ ወደ አማርኛ እንደተረጎመም ይነገርለታል።
ነቢይ የፃፋቸው ግጥሞች ወደ እንግሊዝኛ እና ፈረንሳይኛ የተተረጎሙ ሲሆን፤ በአዲስ አድማስ ጋዜጣ ላይ በተከታታይ ይፅፋቸው በነበሩ "የኛ ሰው በአሜሪካ" የተሰኘው የጉዞ ማስታወሻ ተወዳጅነትን አትርፎለታል።
ነቢይ ሕይወቱ ያለፈው በተወለደ በ68 ዓመቱ ሲሆን የሶስት ሴት ልጆች አባት ነበር። የቀብሩ ሥነ ሥርዓት ባለቤቱ እና ልጁ ከውጭ ሀገር ከመጡ በኋላ እንደሚፈፀም ሸገር ኤፍኤም 102·1 አስደምጧል።

