የእሥራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ናፍታሊ ቤኔት፤ የሩስያ ፕሬዚደንት ቭላድሚር ፑቲን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትራቸውን የአዶልፍ ሂትለር የይሁዲ ዝርያ ንግግር አስመልክተው ይቅርታ መጠየቃቸውን ገለጡ።
የሩስያው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሰርጌይ ላቭሮቭ እሑድ ሜይ 1 'ሂትለር የይሁዲ ዝርያ አለው' ማለታቸው በእሥራኤል ዘንድ የሆሎኮስትን ሰቆቃ ዝቅ የሚያደርግና "ይቅርታ የለሽ ሐሰት" ነው አሰኝቷል።
ሆኖም ፕሬዚደንት ፑቲን በስልክ ይቅርታ በመጠየቃቸው ጠቅላይ ሚኒስትር ቤኔት ይቅርታውን ተቀብለዋል። ምስጋናም አቅርበዋል።
ሁለቱ መሪዎች አያይዘውም ሩስያ እንደምን የዩክሬይን ወደብ ከተማ ማሪዩፖል አዞፍስታህል ብረታ ብረት ማምረቻ ውስጥ አሁንም ድረስ ተጠልለው ያሉ ሰላማዊ ሰዎች ከተባበሩት መንግሥታትና ቀይ መስቀል ጋር በመተባበር ስለተበጀላቸው መተላለፊያ ተነጋገረዋል።
ይህ በእንዲህ እንዳለም የተባበሩት መንግሥታት ቅልፊት ሰላማዊ ሰዎቹን ከተጠለሉበት ለማውጣት ወደ እዚያ አምርቷል።
በሌላም በኩል የዩክሬይን አዞፍ ሬጅመንት ምክትል አዛዥ ስቫያቶስላቭ ፓላማር የሩስያ ጦር ለሶስት ተከታታይ ቀናት ጥቃት እንደሰነዘረባቸው ጠቅሰው፤ ሆኖም አብዛኛውን የማምረቻው አካባቢ በዩክሬይን ቁጥጥር ስር እንዳለ ተናግረዋል።

