ጠቅላይ ሚኒስትር ስኮት ሞሪሰን ጠቅላይ እንደራሴው ዘንድ ቀርበው አገር አቀፍ ምርጫ ለመጥራት ወደ መዲናይቱ ካንብራ እያመሩ ነው።
የምርጫው ቀን ሜይ 21 ይሆናል ተብሎ ይጠበቃል።
አቶ ሞሪሰን መንግሥታቸው ድጋሚ እንዲመረጥ ሲጥሩ 55 - 46 ፐርሰንት በሕዝብ አስተያየት እየመራ ያለው የሌበር ፓርቲ አዲስ መንግሥት ለማቆም እየጣረ ነው።
ፓኪስታን ጠቅላይ ሚኒስትር
የፓኪስታን ተቃዋሚ ቡድን አባላት በጠቅላይ ሚኒስትር ኢምራን ከሃን ላይ አመኔታ የለንም በሚል በአብላጫ የፓርላማ ድምፅ በመስጠት ጠቅላይ ሚኒስትሩን ከኃላፊነታቸው ገፍተው አውርደዋል።
የፓርላማው አፈ ጉባኤ 174 የምክር ቤት አባላት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ላይ አመኔታ እንደሌላቸው ድምፅ መስጠታቸውን አስታውቀዋል።
የጠቅላይ ሚኒስትር ከሃን ደጋፊዎች ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ከስልጣን መገፋት ተቃዋሚዎች ከዩናይትድ ስቴትስ ጋር ተመሳጥረው ነው በሚል ዛሬ እሑድ አገር አቀፍ የተቃውሞ ሰልፍ ያካሂዳሉ።

የተቃዋሚዎቹን ቡድን በዋነኛነት የሚመራው የፓኪስታን ሙስሊም ሊግ የጠቅላይ ሚኒስትርነቱን ሥፍራ ይይዛል።
አቶ ክሃን ዓርብ ዕለት ባደረጉት ንግግር ዩናይትድ ስቴትስን አሌ ብለው ፊታቸውን ወደ ቻይናና ሩስያ በማዞራቸው ተቀናቃኞቻቸው በውጭ ፖሊሲ ምርጫቸው ቅሬታ ካደረባት አሜሪካ ጋር ተመሳጥረው ሊገፏቸው ማሰባቸውን ተናግረዋል።

