የዩናይትድ ስቴትስ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አንቶኒ ብሊንከን ዓለም ላይ ተጋርጠው ያሉ ተግዳሮቶችን ተቋቁሞ ለማለፍ እንደ ዩናይትድ ስቴትስና አውስትራሊያ ያሉ ቀና አመለካከት ያላቸው አገራት አብረው መሥራትን ግድ እንደሚል አሳሰቡ።
አቶ ብሊንከን ዛሬ ሐሙስ ፌብሪዋሪ 10 ሜልበርን አውስትራሊያ የገቡት አውስትራሊያ፣ ዩናይትድ ስቴትስ፣ ጃፓንና ሕንድን ባካተተውና ቻይናን ለመገዳደር በተቋቋመው የአራትዮሽ ስትራቴጂያዊ ስብሰባ ላይ ለመታደም ነው።
አቶ ብሊንከን ዛሬ ጠዋት ሜልበርን ዩኒቨርሲቲ ተገኝተው ተማሪዎችን በዓለም አቀፋዊ ጉዳዮች ዙሪያ አነጋግረዋል።
አክለውም በአውስትራሊያና ዩናይትድ ስቴትስ መካከል ካለው መልክአ ምድራዊ ርቀት ባሻገር በዕሴቶቻቸውና ጥቅሞቻቸው መካከል ያሉ ልዩነቶች ጥቂት መሆናቸውን ገልጠዋል።
"ሙሉ ክትባት"
አውስትራሊያ ውስጥ "ሙሉ ክትባት" መከተብ ማለት ዕድሜያቸው 16 እና ከዚያ በላይ ለሆኑ ሁሉ ሶስት ዙር ክትባቶችን መከተብ ማለት እንዲሆን የአውስትራሊያ ቴክኒካዊ የክትባት አማካሪ ቡድን ወሰነ።
ይህ የተገለጠው የብሔራዊ ካቢኔው በዛሬው ዕለት ያካሔደው ውሳኔ እንዳበቃ ነው።
ሆኖም ውሳኔው እስካሁን ዓለም አቀፍ መንገደኞችን ገና አላካተተም።
በአሁኑ ወቅት ዕድሚያቸው 16 እና ከዚያ በላይ የሆኑ 93.9 ፐርሰንት አውስትራሊያውያን የሁለት ዙር ክትባቶችን ሲከተቡ ባለፉት 14 ሳምንታት 46.3 ፐርሰንቱ ሶስተኛ ዙር ክትባት ተከትበዋል።
አዲሱ የሙሉ ክትባት ውሳኔ ወደ ሶስት ዙር ክትባት ከፍ ማለትን አስመልክቶ ኩዊንስላንድና ቪክቶሪያ ተመሳሳይ የሙሉ ክትባት ደረጃን በዓለም አቀፍ መንገደኞች ላይም ለመጣል አስበዋል።
የኒው ሳውዝ ዌይልስ ፕሪሚየር በበኩላቸው የክትባት ባለስልጣኑን ውሳኔ ተከትለው ከውሳኔ ላይ እንደሚደርሱ ጠቁመዋል።

