የአውስትራሊያ መከላከያ ሚኒስትር ሪችድ ማርልስ በሲንጋፖር ዓለም አቀፍ የመከላከያ ሚኒስትራት ጉባኤ ላይ በተካሔደ የትውውቅ ሥነ ሥርዓት ከቻይና አቻቸው ጄኔራል ዌይ ፌንግሂ ጋር እጅ ለእጅ በመጨባበጥ ተዋውቀዋል።
የቻይናና አውስትራሊያ ግንኙነት ቅዝቃዜ ከገባው ከሁለት ዓመታት በኋላ የሁለቱ አገራት የመከላከያ ሚኒስትሮች ለስብሰባ በአንድ ላይ ሲታደሙ ይህ የመጀመሪያው ጊዜ ነው።
መከላከያ ሚኒስትር ማርልስ ከጄኔራል ዌይ ጋር ያደረጉት ግንኙነት ከእጅ ለእጅ መጨባበጥ የዘለለ የትውውቅ ሥነ ሥርዓት እንጂ የሰከነ የሁለትዮሽ ንግግር ባለመሆኑ ከዚያ በላይ አግኖ ማየት እንደማያሻ ተናግረዋል።
ይሁንና ሲንጋፖር ሻንግራይ-ላ እየተካሔደው ያለው ጉባኤ አንድ ተጨማሪ ቀን ስለሚቀረው ከቻይናው አቻቸው ጋር ምናልባትም በወጉ ተገናኝቶ የመነጋገር ዕድል ሊኖር እንደሚችል ጠቁመዋል።
አቶ ማርልስ እንዲህ ባለ ውስብስብ ጊዜ ዓለም አቀፍ ግንኙነት "በረጋ፣ ሙያዊ በሆነና መከባበርን በተላበሰ" መልኩ ሊካሄድ እንደሚገባ አሳስበዋል።
ሆኖም አውስትራሊያ ብሔራዊ ጥቅሞቿን አስመልክቶ ሉላዊ ሥርዓተ ደንብን በተከተለ መንገድ እንዲከወን ለማስደረግ ወደ ኋላ እንደማትልም ገልጠዋል።
በሌላም በኩል መከላከያ ሚኒስትሩ ከፈረንሳዩ አቻቸው ሰባስቲያን ሌኮርኑ ጋር ተገናኝተው ተነጋግረዋል።
ሁለቱ ሚኒስትራት ንግግራቸው አዎንታዊነት የመላውና ባለፈው የስኮት ሞሪሰን መንግሥት ወቅት በባሕር ሰርጓጅ መርከብ ውል ስረዛ ሳቢያ ሻክሮ የነበረውን ግንኙነት በአዲስ መልክ ለመጀመርም ቃል ተለዋውጠዋል።

.ይህ በእንዲህ እንዳለም፤ የዩናይትድ ስቴትስ መከላከያ ሚኒስትር ሎይድ ኦስቲን ምንም እንኳ ቻይና በኢንዶ-ፓስፊክ ቀጣና ይበልጡኑ ግፊቷ እየጠነከረ ያለ ቢሆንም በዋሽንግተንና ቢጂንግ መካከል ተፈጥረው ያሉትን ውጥረቶች ለማርገብና ግጭት እንዳይፈጠር ከወዲሁ ለመግታት ጥረት እንደምታደርግ ተናግረዋል።
ሁለቱ የዓለም ታላላቅ ባለ ምጣኔ ሃብት አገራት በተለይም በታይዋን፣ በቻይና የሰብዓዊ መብቶች ሬኮርድና የደቡብ ቻይና ባሕር እንቅስቃሴዎችን በተመለከተ በመካከላቸው ውጥረቶች ሰፍነው አሉ።

አቶ ኦስቲን በቻይናና ዩናይትድ ስቴትስ መካከል ተፈጥረው ያሉትን ውጥረቶች አርጋቢ ብልሃቶችን ለማፈላለግ ከጄኔራል ዌይ ጋር ዓርብ ዕለት ተገኛኝተው ለአንድ ሰዓት ያህል የተነጋገሩ ቢሆንም ችግር ፈቺ እልባት ላይ ሳይደርሱ ተለያይተዋል።

