የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን ግንቦት 4 - 2014 በሶማሌ ክልል ፋፈን ዞን ጉርሱም ወረዳ ቦምባስ ከተማ መጋቢት 11 እና 12 ቀን 2014 ዓ.ም. በባሕላዊ ሥነ ሥርዓት የጎሳ መሪ (ሱልጣን) ለመምረጥ ታድመው ከነበሩት ውስጥ 11 ሰዎች በክልሉ ፀጥታ ኃይሎች እና በታጣቂ ግለሰቦች በተፈጸመባቸው ጥቃቶች ሕይወታቸው ማለፉን አስታወቀ።
ኮሚሽኑ ግድያ እና የአካል ጉዳት ስለመፈጸሙ የደረሰው ጥቆማ ተከትሎ ከሚያዝያ 7 እስከ 12 ቀን 2014 ዓ.ም. በቦታው በመገኘት ምርመራ ማካሔዱንም ገልጧል።
የምርመራ ውጤቱም በታጠቁ ሰዎች ግድያዎች መፈፀማቸውንና በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች ከመጠን ያለፈ የኃይል አጠቃቀም ( excessive use of lethal force) የደረሰ መሆኑን፤ በተጨማሪም ቢያንስ በ33 ሰዎች ላይ ቀላልና ከባድ የአካል ጉዳት መድረሱን ኮሚሽኑ በምክንያታዊ ሁኔታ አሳማኝ (reasonable ground to believe) መሆኑን አመልክቷል።
አያይዞም፤ የአካል ጉዳት ከደረሰባቸው ሰዎች መካከል በቡሽማን ቀበሌ 7 ተጎጂዎችን በቤታቸው፣ እንዲሁም በጅግጅጋ አጠቃላይ ሆስፒታል በመገኘት በመታከም ላይ የነበሩ 5 ተጎጂዎችን በማነጋገር እና ምልከታ በማድረግም ማስረጃ ያሰባሰበ መሆኑን ገልጧል፡፡
በተጨማሪም ቦምባስ ከተማ የሚገኝ የጥቃቱ ሰለባዎች የተቀበሩበትን የመቃብር ስፍራ የጎበኘ ሲሆን፣ በዚህም በመጀመሪያ ቀን ሕይወታቸው ያለፈ ሰዎች የተቀበሩበት አንድ የጅምላ መቃብር እና በሁለተኛው ቀን የተገደለች ሴት የተቀበረችበት መሆኑ የተገለጸ ለብቻው ያለ አንድ ሌላ የመቃብር ቦታ ተመልክቷል፡፡
ኮሚሽኑ ከክልሉ የመንግሥት አካላት የክልሉ ፕሬዚዳንት ጽሕፈት ቤት እና የክልሉ ፖሊስ ኮሚሽን ኢሰመኮን ያነጋገሩ ሲሆን፣ የክልሉ ልዩ ኃይል፣ የክልሉ የፀጥታ ቢሮ እና የጉርሱም ወረዳ አስተዳደርን ለማግኘት የተደረገው ተደጋጋሚ ጥረት ባለመሳካቱ ምላሻቸውን ማካተት አልተቻለም።
የኢሰመኮ ዋና ኮሚሽነር ዶ/ር ዳንኤል በቀለ የክልሉ መንገግሥት በፀጥታ ኃይሎች የተፈጸመው ግድያ ፈጽሞ ተገቢ እንዳልነበር በመገንዘብ ለተጎጂዎችና ቤተሰቦች ካሳ እንዲከፈል ማድረጉ ጥሩ እርምጃ መሆኑን አስታወስው፤ “ከዚህ በተጨማሪ የተሟላ ፍትሕ ለማረጋገጥና ለወደፊትም ተመሳሳይ የሰብአዊ መብቶች ጥሰቶች እንዳይከሰቱ ለመከላከል የወንጀል ተጠያቂነትን ማረጋገጥ ይገባል፤ ስለሆነም በአፋጣኝ የወንጀል ምርመራ ሊጀመር ያስፈልጋል” ብለዋል፡፡

