የቀድሞው ፕሬዚደንት ትራምፕ ደጋፊዎች ጃኑዋሪ 6 ካፒቶል ሂል ላይ ለፈጸሙት ጥቃት አነሳሽ ተደርገው የተከሰሱት ትራምፕ በፓርቲያቸው ድጋፍ በጥፋተኝነት ከመፈረጅ ድነዋል።
አምስት ቀናት ባስቆጠረው የሕግ መወሰኛ ምክር ቤት ችሎት ስሚ ከዲሞክራቲክ ፓርቲ ጋር ወግነው ድምፃቸውን የሰጡ የሪፐብሊካን ፓርቲ አባላት ሰባት ብቻ በመሆናቸው አቶ ትራምፕ በጥፋተኝነት ሳይፈረጁ ቀርተዋል።
በዲሞክራቲክ ፓርቲ በኩል ውሳኔውን አስመልክቶ የዩናይትድ ስቴትስ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈ ጉባኤ ናንሲ ፔሎሲ "ሥራቸውን ያልተወጡ፣ ሕገ መንግሥቱን ያላስከበረ የፈሪዎች ቡድን ዶናልድ ትራምፕ ከጥፋተኝነት አትርፏል" ሲሉ፤ የሪፐብሊካኑ የሕግ መወሰኛ ምክር ቤት መሪ ሚች ማክኮነል ዶናልድ ትራምፕ ለጃኑዋሪ 6ቱ ጥቃት "በግብርና በሞራል ተጠያቂ ናቸው" ብለዋል።
ከተጠያቂነት በማምለጣቸው እፎይታና የልብ ልብ የተሰማቸው ዶናልድ ትራምፕ ግና " የኛ አሜሪካን ዳግም ታላቅ የማድረግ ውብ፣ ታሪካዊና የአርበኝነት ንቅናቄ ገና መጀመሩ ነው" በማለት ለደጋፊዎቻቸው መልዕክታቸውን ያስተላለፉ ሲሆን፤ አክለውም በመጪዎቹ ወራቶች ውስጥ የሚያጋሯቸው ጉዳዮች እንዳሉ ጠቁመዋል።
ቪክቶሪያ
የቪክቶሪያ የንግድ ባለቤቶች ለአምስት ቀናት በተጣለው የኮሮናቫይረስ ገደብ ሳቢያ የቫለንታይንና ሉናር ዓዲስ አመት ዝግጅት ገቢያቸው ላይ ጉዳት አድርሶ እንደሚያልፍ ገለጡ።
የላቨር ሬስቶራንት ባለቤት ገደቡ ዊል ኒውተን እስከ 40,000 ዶላርስ ገቢ እንደሚያሳጣቸው ሲናገሩ፤
"ፍጹም ልብ ሰባሪ ነው። የቫለንታይንን ቀን ለማክበር ብቻ 148 የስልክ ጥሪዎችን ተቀብያለሁ። በእዚህ ዓመት እስከሚቀጥለው ሳምንት ድረስ የቫለንታይን ዝግጅት ማድረግ አንችልም ብሎ መንገሩ በጣሙን አዋኪ ነው። ከዚህም በተጨማሪ ትርፍ ሚሆኑት የምግብና መጠጥ ትዕዛዞች ጉዳይ አለ። ሁለት መቶ ያህል ኦይስተሮች ማቀዝቀዣዎች ውስጥ አሉን። ኛ በሁለት እግሮቻችን ልንቆም ነው ብለን ስንል ይህ ገጥሞናል። ለዚህ ያዘጋጀነው አማራጭ ዕቅድ የለንም" ብለዋል።

