የአውስትራሊያ ኃይል ተቆጣጣሪ የኃይል ማመንጫ ጂኔሬተሮች ላይ ላልተወሰነ ጊዜ እገዳ በመጣል ገበያውን ተቆጣጠረ።
የአውስትራሊያ ኃይል ገበያ ኦፕሬተር እርምጃውን የወሰደው አስተማማኝ የኃይል አቅርቦት እንዳይቋረጥ ለማስቻል መሆኑን አስታውቋል።
ቀደም ሲል የተወሰኑ ኩባንያዎች የኃይል ተቆጣጣሪው የጣለውን የዋጋ ተመን ጣራ በመጋፋት አቅርቦታቸውን አቋርጠው ነበር።
የኃይል ተቆጣጣሪው እርምጃ በመንግሥት በኩል ድጋፍ ያስገኘለት ሲሆን፤ ሲልም የኃይል ሚኒስትር ክሪስ ባወን ተቆጣጣሪው የኃይል አቅርቦት መቋረጥ እንዳይከሰት አስፈላጊውን እርምጃ እንደሚወስድና የአውስትራሊያ ኃይል ተጠቃሚዎችን ፍላጎት ለማስጠበቅ ሲል ለሚወስዳቸው እርምጃዎችም መንግሥታቸው ሙሉ ድጋፉን እንደሚቸረው አስታውቀዋል።
በሌላም በኩል የኒው ሳውዝ ዌይልስና የኩዊንስላንድ የኢነርጂ ሚኒስትሮች የኃይል ተቆጣጣሪውን እርምጃ መደገፋቸውን ገልጠዋል።
ዝቅተኛ ደመወዝ
ጠቅላይ ሚኒስትር አንቶኒ አልባኒዚ የፍትሕ ሥራ ኮሚሽን ለዝቅተኛ ደመወዝ ተከፋዮች የ5.2 ፐርሰንት ጫማሪ ማድረጉ በጣሙን ያስደስታቸው መሆኑን ተናገሩ።
ጭማሪው እስካሁን የነበረውን ብሔራዊ ዝቅተኛ ደመወዝ መጠን ከ $20.33 ወደ $21.38 በሰዓት ከፍ በማድረግ ተከፋዮች በሳምንት የ $40 ጭማሪ እንዲያገኙ ያስችላል።

አቶ አልባኒዚ የአውስትራሊያ ዝቅተኛ ደመወዝ ተከፋዮች ጭማሪው ተገቢያቸው ነው ሲሉም መልካምነቱን አንስተዋል።
አክለውም "እውነታው አብዛኛዎቹ የዝቅተኛ ደመወዝ ተከፋዮች የወረርሽኙ ወቅት ጀግኖቻችን ናቸው። እኒህ ሠራተኞች ከምሥጋና ቃሎቻችን በላይ ሊያገኙ ይገባቸዋል። እነሆም ዛሬ የደመወዝ ጭማሪ አግኝተዋል" ብለዋል።
በሌላም በኩል የአውስትራሊያ ሠራተኞች ምክር ቤት ፀሐፊ ሳሊ ማክማነስ የደመወዝ ጭማሪው የአውስትራሊያ 25 ፐርሰንት የሠራተኞች አካል በሆኑት በ 2.6 ሚሊየን ሠራተኞች ዘንድ በመላክማ ጎኑ ተቀባይነትን እንዳለው ተናግረዋል።
ይሁንና በአሠሪዎች ቡድናት በኩል ግና ጭማሪው ምጣኔ ሃብቱን ለአደጋ ተጋላጭ ሊያደርገው እንደሚችልና በተለይም በመስተንግዶው መስክ ላሉቱ ጭማሪውን የሚያገኙት ዘግይተው እንደሚሆን አሳስበዋል።
የአውስትራሊያ ንግድና ኢንዱስትሪ ምክር ቤት በደመወዝ ጭማሪው ሳቢያ ሸማቾች ከፍ ያለ ዋጋ ሊከፍሉ እንደሚችሉ ከወዲሁ አስጠንቅቋል።
ምክር ቤቱ ጫማሪው በንግዱ ላይ የ 7.9 ቢሊየን ዶላር ወጪን እንደሚያክልና የዋጋ ግሽበትንም ሊያባብስ እንደሚችል አመላክቷል።
ኒውዝላንድና ሰለሞን ደሴቶች
የአውስትራሊያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ፔኒ ዎንግ በዚህ ሳምንት የቀጣና ፀጥታና የአየር ንብረት ለውጥ ላይ ለመምከር ወደ ኒውዝላንድና ሰለሞን ደሴቶች ያቀናሉ።
ሴናተር ዎንግ ነገ ሐሙስ ጁን 16 / ሰኔ 9 ወደ ዌሊግተን አቅንተው ከኒውዝላንዷ አቻቸው ጋር ተገናኝተው ይመክራሉ።

በቀጣዩ ቀን ዓርብ ጁን 15 / ሰኔ 10 ወደ ሰለሞን ደሴቶች በማምራት ከጠቅላይ ሚኒስትር ማናሴህ ሶጎቫሬ ጋር ይወያያሉ።

