ቪክቶሪያ በ$5.3 ቢሊየን 12,000 አዲስ የጋራ መኖሪያ ቤቶችን ልትሠራ ነው

*** በሺህዎች የሚቆጠሩ የቀኝ አክራሪዎች ዶናልድ ትራምፕን ደግፈውና የፕሬዚደንታዊ ምርጫ ውጤቱን ተቃውመው በዋሽንተንግተን ከተማ ተመሙ

Amharic News 15 November 2020

A public housing tower in North Melbourne while it was under strict lockdown in Melbourne on Saturday, July 18, 2020. Source: AAP

የቪክቶሪያ መንግሥት ሜልበርን ከተማና ሪጂናል ቪክቶሪያ ውስጥ በ$5.3 ቢሊየን 12,000 አዲስ የጋራ መኖሪያ ቤቶችን ለመሥራት ውጥን መንደፉን አስታወቀ።

ኖቬምበር 24 ይፋ በሚሆነው የ2020/21 ስቴት በጀት ውስጥ የታቀፈው ይኼ ዕቅድ 9,300 አዳዲስ ቤቶች የሚገነባና 1,100 አሁን ያሉ የጋራ መኖሪያ ቤቶችን የሚተካ ይሆናል።    

የቪክቶሪያ ፕሪሚየር ዳንኤል አንድሩስ እንዳሉት 2,000 አዲስ የሚገነቡት የጋራ መኖሪያ ቤቶች በአዕምሮ ሕመም ለተጠቁ፣ 2,900 በመጠነኛ ወጪ ተገንብተው ዝቅተኛ ገቢ ላላቸው ሰዎች መኖሪያ ይሆናሉ።

በተጨማሪም ከሚገነቡት ቤቶች ውስጥ 1,000 የሚሆኑት የቪክቶሪያ ነዋሪ ለሆኑ ነባር ዜጎች እንዲሁም ሌላ 1,000 ቤቶች የቤት ውስጥ ጥቃት ሰለባ ለሆኑ መኖሪያ እንደሚሆኑ ፕሪሚየር አንድሩስ ተናግረዋል።  

አያይዘውም፤ ፕሮግራሙ 10,000 ያህል ሥራዎች በየዓመቱ ለአራት ዓመታት እንደሚፈጥርና 6,000 መኖሪያ ቤቶችም በ18 ወራት ተሠርተው እንደሚጠናቀቁ ተናግረዋል። 

የቤቶች ሚኒስትር ሪችድ ዌይን በበኩላቸው 25 ፐርሰንቱ የበጀቱ ድጎማ ለሪጂናል ቪክቶሪያ እንደሚውል ገልጠዋል።

የዩናይትድ ስቴትስ ምርጫ

የቀኝ ፅንፈኞች ሚሊሺያዎችና ፕራውድ ቦይስ አብረው በተመሙበት የመዲናይቱ ዋሽንግተን በጠቅላይ ፍርድ ቤት ፊት ለፊት ሰልፍ ከሚወጡ የጸረ - ትራምፕ ሰልፈኞች ጋር ግጭት እንዳይቀሰቀስ ለመቆጣጠር ግዙፍ የሆነ የጸጥታ አስከባሪ ሃይልም ተገኝቷል።

ለትራምፕ ደጋፊዎች ሰልፍ መውጣት አስባብ የሆነው ዶናልድ ትራምፕ 'የምርጫ ማጭበርበር ተፈጽሞ ድሌን ተነጥቄያለሁ' ሲሉ ማስረጃ አልባ እሮሮ ማሰማታቸውን ተከትሎ ነው።

አቶ ትራምፕም ድጋፋቸውን ለማሳየት ሰልፈኞቹ በተገኙበት አደባባይ በሞተረኛ በታጀበ አውቶሞቢላቸው አቋርጠዋል።

በወቅቱም ሰልፈኞቹ የድጋፍ ጩኸትና ፉጨት አሰምተዋል። ባንዲራዎቻቸውንም አውለብልበዋል። "ታይቶ የማይታወቅ ምርጥ ፕሬዚደንት"፣ "ስርቆት ይቁም"፣ "አራት ተጨማሪ ዓመት" ሲሉም ድምጻቸውን አስተጋብተዋል።  

Amharic News 15 November 2020
With the US Capitol in the background, supporters of President Donald Trump rally at Freedom Plaza, Saturday, Nov. 14, 2020, in Washington. Source: AAP

እስካሁን ይፋ በሆኑት የምርጫ ውጤቶች የትራምፕ ተቀናቃኝ የነበሩት የዲሞክራቱ ጆ ባይደን 306 የምርጫ ኮሌጅ ድምፆችን ሲያገኙ አቶ ትራምፕ 232 አግኝተዋል።

አንድን ፕሬዚደንታዊ ዕጩ ለፕሬዚደንትነት የሚያበቁት 270  የምርጫ ኮሌጅ ድምፆች ናቸው። 

 

 


2 min read

Published

By NACA

Presented by Kassahun Seboqa Negewo


Share this with family and friends


Follow SBS Amharic

Download our apps

Watch on SBS

SBS World News

Take a global view with Australia's most comprehensive world news service

Watch now