የአውስትራሊያው ጠቅላይ ሚኒስትርና የቻይናው ፕሬዚደንት ሺ ጂንፒንግ ባሊ - ኢንዶኔዥያ እየተካሔደ ባለው የቡድን 20 ጉባኤ ላይ ተገናኝተው ተነጋገሩ።
ከ2016 ወዲህ በአውስትራሊያና ቻይና መሪዎች መካከል ይፋ የመሪዎች ግንኙነት ሲካሔድ ይህ የመጀመሪያው ነው።
ሁለቱ መሪዎች ተገናኝተው የተነጋገሩት ኑሳ ዱዋ ባሊ በሚገኘው ሙሊያ የቅንጦት ሪዞርት ውስጥ ነው።

ሁለቱ መሪዎች ገንቢ የሆነ ውይይት ማድረጋቸውን ጠቅላይ ሚኒስትሩ ገልጠዋል።
ፕሬዚደንት ሺም በበኩላቸው ባለፉት ዓመታት በቻይናና አውስትራሊያ መካከል የነበሩት ግንኙነት ሊያዩት በማይሹት መልኩ አዋኪ እንደነበር ጠቅሰው፤ ሆኖም ጠቅላይ ሚኒስትር አልባኒዚ ደጋግመው ከቻይና ጋር አስተውሎት የተመላበት ግንኙነት ማድረግ እንደሚሹ መናገራቸውን እንደተረዱና በዚያ የተሳቡ መሆኑን ገልጠዋል።
የሁለቱ አገራት ግንኙነቶች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉና በሳቢያውም ቻይና በአውስትራሊያ ላይ ጥላ ያለችው የምጣኔ ሃብት ማዕቀብ ሊነሳ ይችላል የሚል ተስፋን አሳድሯል።
በ1972 የተጀመረው የአውስትራሊያና ቻይና ግንኙነት በመጪ ወርኅ ዲሴምበር 50ኛ ዓመቱን ያስቆጥራል።

