የሀገር ሽማግሌዎቹ ወደ መቀለ የሚሔዱት በራሳቸው ተነሳሽነት ሲሆን የሀይማኖት መሪዎች፤ ታዋቂ ሰዎች፤ ምሁራን የተካተቱበት መሆኑን አውሎ ሚዲያ ደርሶኛል ያለው መረጃ ያሳያል።
እንደ መረጃው ከሆነ ሊቀ ጳጳስ አቡነ ማትያስ ቀዳዊ ፤ ብፁዕ ካርዲናል ብርሐነእየሱስ፤ ተቀዳሚ ሙፍቲ ሀጂ ፤ ፓስተር ፃዲቁ አብዶ፤ ፓስተር ታደሰ አዱኛ፤ ዶክተር ዮናስ ይገዙ ፤ ዶክተር እያሱ ኤሊያስ እንዲሁም ከታዋቂ ሰዎች ደግሞ አትሌት ሺ አለቃ ሀይሌ ገብረስላሴን ጨምሮ 52 ሰዎች ናቸው በፈቃዳቸው ወደ ትግራይ የሚሔዱት።
የጉዞው ዋና አላማም ባለፉት ሁለት አመታት በትግራይ ክልል መንግስት እና በፌዴራል መንግስት መካከል እየተፈጠረ ያለው ልዩነት በህዝቦች አንድነት ላይ እየተፈጠረ ያለው መቃቃር ለማስቀረትና ለማጥበብ በሚቻልባቸው ጉዳዮች ላይ ለመምከር ነው።
ቡድኑ በትግራይ በሚኖረው ቆይታ ከክልሉ መሪዎች ፤ የሀገር ሽማግሌዎችና ተወካዮች ጋር እርቅና መግባባት እንዲፈጠር በሚያስችሉ ጉዳዮች ላይ ይመክራል ነው የተባለው።
በተለይም በፖለቲካ ሀይሎች መካከል ያለው አለመግባባት በህዝቦች ነባርና የቆየ ግንኙነት ላይ እየፈጠረ ያለው ጫና እየሰፋ በመሆኑ የትግራይ ክልል መንግስትና የፌዴራል መንግስት ወደ መግባባት የሚመጡበትን መንገድ ላይ በዋናነት ይመክራል ተብሎ ይጠበቃል።

