በኮቪድ-19 ወረርሽኝ ሳቢያ የአውስትራሊያ ዓለም አቀፍ ድንበር በመዘጋቱ እገዳ ተጥሎበት የነበረው የክሩዝ መርከብ ጉዞ ዳግም ፈቃድ በማግኘቱ የቱሪዝም ኢንዱስትሪ ደስታውን ገለጠ።
መንገደኞችን የጫኑ መርከቦች የጥንቃቄ ደንቦችን ግብር ላይ በማዋል ከዛሬ እሑድ ኤፕሪል 17 ጀምሮ ወደ አውስትራሊያ መቅዘፍ ይችላሉ።
በጤና ጥንቃቄዎቹ መሠረትም ተሳፋሪዎች የፊት ጭምብሎችን ማጥለቅ፣ የኮቪድ-19 ምርመራዎችን ማድረግና ሙሉ ክትባቶችን መከተብ ይጠበቅባቸዋል።
የመጀመሪያዋ ደራሽ መርከብ Pacific Explorer ስትሆን፤ ነገ የሰኞ ፋሲካ ዕለት ሲድኒ ትደርሳለች።
የቱሪዝም ኒው ሳውዝ ዌይልስ ተጠሪ ግሬግ ቢኒስኪን የመንገደኞች መርከቦቹ ዳግም ወደ አውስትራሊያ መመለስ ለቱሪዝም ኦፕሬተሮች በእጅጉ አስፈላጊ መሆኑን ለSBS ገልጠዋል።

