ከጁላይ 15 - 16 ለሁለት ቀናት ባሊ - ኢንዶኔዥያ የተካሔደው የቡድን - 20 የፋይናንስ ሚኒስትሮች ስብሰባ የዩክሬን ጦርነትን አስመልክቶ በታዳሚ አገራት የአቋም መለያየት ሳቢያ የጋራ አቋም መግለጫው ውስጥ ሳያካትት አክትሟል።
የዩናይትድ ስቴትስ በጅሮንድ ጃኔት የለን የጋራ መግለጫው ላይ የዩክሬይን ጦርነትን አስመልክቶ አንድ ዓይነት አቋም መያዝ ያልተቻለው የተላያዩ አገራት ተመሳሳይ ዕይታዎችን ባለማንፀባረቃቸው እንደሆነ ገልጠዋል።
ሆኖም በስብሰባው መዝጊያ ላይ የወቅቱ የቡድን - 20 ሰብሳቢ የሆነችው ኢንዶኔዥያ ፋይናንስ ሚኒስትር ስሪ ሙሊያኒ ምጣኔ ሃብት ላይ ባተኮረውና በሉላዊ ጉዳዮች "ጠንካራ ሉላዊ መግባባት" እንደሚያሻ ባመላከተው የፋይናንስ ሚኒስትሮችና የማዕከላዊ ባንክ ገዢዎች መግለጫ ላይ በታካይነት የዩክሬይን ጦርነትን አስመልክቶ የተነሱ የተለያዩ አተያዮች እንዲንፀባረቁ አድርገዋል።
በሚኒስትሮቹ ስብሰባ ወቅት ምዕራባውያን አገራት በሩስያ ላይ ጠንካራ ማዕቀቦችን መጣልንና ሩስያን በዩክሬይን ጦርነት በጦር ወንጀሎች ተጠያቂ መሆንን ሲያነሱ፤ ቻይና፣ ሕንድና ደቡብ አፍሪካ አቋማቸውን በዝምታ ምላሽ አንፀባርቀዋል።
በጅሮንድ የለን በቡድን - 20 ሚኒስትሮች ዘንድ ያሉ ልዩነቶች እንዳሉ ሆነው እየከፋ በመሔድ ላይ ያለውን የምግብ ዋስትና ቀውስ ለመግታት የጋራ ስምምነት ላይ መድረሳቸውን አመላክተዋል።

US Secretary of Treasury Janet Yelle. Source: Getty
በስብሰባው ላይ የዩክሬይን ተወካይ በተጋባዥነት ተገኝተዋል።
ቀጣዩ የቡድን - 20 አራተኛው ዙር ስብሰባ ኦክቶበር 2022 ዋሽንግተን ዲሲ - ዩናይትድ ስቴትስ ውስጥ ይካሔዳል።
የፊት ጭምብል
የክፍለ አገራት መሪዎች አውስትራሊያውያን የኮቪድ - 19 መስፋፋትን ለመገደብ የፊት ጭምብሎችን እንዲያጠልቁ የማሳሳቢያ ጥሪዎችን እያቀረቡ ነው።
ለማሳሳቢያ ጥሪዎቹ አስባብ የሆነውም በትናንትናው ዕለት የታደመው ብሔራዊ ካቢኔ የፊት ጭምብል ማጥለቅን ግዴታ የሚያደርገውን ድንጋጌ ግብር ላይ ለማዋል ከይሁንታ ስምምነት ላይ መድረስ ባለመቻሉ ነው።
በተወሰኑ ክፍለ አገራት ክረምቱ ለኮሮናቫይረስ መስፋፋት አስተዋፅዖ ስለሚኖረው ያለ መከላከያ እርምጃዎች የኮሮናቫይረስ ተዛማችነት ከሚገመተው በላይ ሊሆን ይችላል የሚል ስጋትን አሳድሯል።
የደቡብ አውስትራሊያ ተጠባባቂ ፕሪሚየር ሱዛን ክሎዝ በኮቪድ - 19 ተጠቅተው ሆስፒታል የሚዳረጉ ሰዎች ቁጥር ከጁላይ ወር መጨረሻ ላይ ሊያሻቅብ ይችላል የሚል ስጋት በመንግሥት ዘንድ ያደረ መሆኑን ገልጠዋል።
የፊት ጭምብሎችን የማጥለቅ ጥሪ በጤና ባለሙያዎች ዘንድ ድጋፎችን አግኝቷል።

Victorian Health authorities are recommending residents resume wearing face masks indoors as COVID-19 infections begin to rise again across Australia. Source: Getty
የአውስትራሊያ የሕክምና ባለሙያዎች ማኅበር ፕሬዚደንት ዶ/ር ኦማር ኮሺድ አዲስ የኮሮናቫይረስ ማዕበል አገሪቱን በመታበት ወቅት የፊት ጭምብል ድንጋጌን ግብር ላይ ማዋል አስፈላጊ እንደሆነ አፅንዖት ሰጥተው አሳስበዋል።