የኢፌዴሪ ጠቅላይ ዐቃቤ ሕግ በሕወሓት አባላት ላይ ክስ መመስረቱን አስታወቀ።
ክስ የተመሰረተባቸው ተከሳሾች የሕዝባዊ ወያኔ ሓርነት ትግራይ ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባላት ውሳኔ በመስጠት ከፍተኛ ተሳትፎ የነበራቸው የህወሀት ማዕከላዊ ኮሚቴ አባላትና የክልልመንግስቱ ካቢኔ አባላት እንዲሁም በትጥቅ ጥቃት ላይ ከፍተኛ ሚና የነበራቸው የኢፈርት ድርጅቶች፣ የግልና የመንግስት ድርጅት አመራሮች፣ የትግራይ ምርጫ ኮሚሽን አመራር አባላት፣ በትግራይ በተካሄደው ኢ-ሕገ-መንግስታዊ ምርጫ ላይ ተሳትፎ ያደረጉት ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች፣ ሊቃነ-መናብርትና የቀድሞ የሕወሓት ከፍተኛ አመራር የነበሩ ታዋቂ ግለሰቦች ናቸው፡፡
ክሱ የተመሰረተው በሁለት የወንጀል አንቀፆች ስር ሲሆን የመጀመሪያው በኃይል፣ በዛቻ፣ በአድማና ሕገ-ወጥ በሆነ መንገድ ኢ-ሕገመንግስታዊ ምርጫ በማካሄድ በሕገ-መንግስት የተቋቋመና እውቅና ያለው የክልል መንግስት መለወጥ በኢ.ፌ.ዴ.ሪ የወንጀል ህግ አንቀጽ 238 ስር የተደነገገውን በመተላለፍ ሲሆን፤ በሁለተኛ ክስ የፌዴራሉን መንግስት በሀይል ለመለወጥ በማሰብ ከ2011 ዓ.ም ጀምሮ የፌዴራል መንግስትን በመሳሪያ ጥቃት መለወጥ የሚችል የትግራይ ወታደራዊ ኮማንድ የተባለ የጦር ሀይል በማደራጀት የፌዴራል መንግስት የሀገር መከላከያ ሰራዊቱ ላይ ጥቃት በማድረስ የሽብር ወንጀልን ለመከላከል የወጣውን አዋጅ አዋጅ ቁጥር 1176/2011 አንቀጽ 3/1እና 3/2 በመተላለፍ ወንጀል ነው፡፡
ጠቅላይ ዐቃቤ ሕግ ለክሱ አስረጅነት 510 የሰው ምስክሮችን እና እና 5329 ገጽ የሰነድ ማስረጃዎችን በማያያዝ ለፍርድ ቤቱ ቅርቧል፡፡
የፌዴራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት የሕገ-መንግስትና የሽብር ወንጀሎችን የሚያየው 1ኛ ችሎት ክሱን በመዝገብ ቁጥር 27128102 በመቀበል በማረሚያ ቤት የሚገኙ ተከሳሾችን ማረሚያ ቤቱ እንዲያቀርብ ቀሪ ተከሳሾችን የፌዴራል ፖሊስ መጥሪያ አድርሶ እንዲያቀርብ በማዘዘዝ ለሐምሌ 26 ቀን 2013ዓ.ም ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
(የፌ/ጠ/ዐ/ህግ)

