የዩናይትድ ስቴትስ ፕሬዚደንት ጆ ባይደን የሩስያውን ፕሬዚደንት ለመጀመሪያ ጊዜ 'የጦር ወንጀለኛ' ብለው ጠሩ። ፕሬዚደንቱ ይህንን ያሉት በዋይት ሃውስ ምስራቅ ክንፍ ከጋዜጠኞች ጋር እየተነጋገሩ ሳለ ነው።
እስካሁን የሩስያና የዩክሬይን ጦርነትን በተመለከተ የጦር ወንጀል መፈጸምን የሚመለከት ምርመራ እየተደረገ ባለበት ወቅት ዋይት ሃውስ "የጦር ወንጀል" የሚሉትን ቃላቶች ላለመጠቀም ሲጥር ቆይቷል።
የክሬምሊን ቃል አቀባይ ዲሚትሪ ፔስኮቭ በበኩላቸው የፕሬዚደንት ባይደን ፕረዚደንት ፑቲንን በጦር ወንጀለኛነት መፈረጅ "ተቀባይነት የሌለውና ይቀር የማይባል አመኔታ የለሽ አባባል" ነው ሲሉ የአጸፋ ምላሽ ሰጥተዋል።
በሌላ በኩል የዩክሬይን ፕሬዚደንት ቮሎድሚር ዜሌንስኪ አሜሪካ ላይ የደረሱትን የፐርል ወደብና የሴፕቴምበር 11 ጥቃቶችን አንስተው ለአሜሪካ ኮንግረስ ባሰሙት ንግግር በድጋሚ የዩክሬይንን አየር ክልል ዝጉልን ጥያቄያቸውን አንስተዋል።
አክለውም፤ ፕሬዚደንት ባይደን በዓለም ላይ ለሰላም መስፈን የበኩላቸውን ጥረት እንዲያደርጉ ጥሪ አቅርበዋል።
ዩናይትድ ስቴትስ የቀጥታ የዩክሬይን የአየር ክልል መዝጋት ተሳትፎ ከሩስያ ጋር ለጦርነት ሊዳርጋት እንደሚችል ደግማ አስገንዘባለች።
ሆኖም አቶ ባይደን ለዩክሬይን "የረጅም ርቀት ተወንጫፊ" ፀረ አውሮፕላን መሳሪያዎችን ጨምሮ ለአዲስ የጦር መሳሪያዎች መግዣ የሚውል እስከ $1 ቢሊየን (A$1.37 ቢሊየን) ልገሳ አድርገዋል።
የኒው ሳውዝ ዌይልስ ፕሪሚየር
የኒው ሳውዝ ዌይልስ ፕሪሚየር ዶሚኒክ ፔሮቴይ እና ባለቤታቸው ሄለን ሰባተኛ ልጃቸውን ሰሌስት ግሬስን መወለድ አበሰሩ።
ሰሌስት ግሬስ የተወለደችው ትናንት ማርች 16 ምሽት ላይ ነው።
ፕሪሚየር ፔሮቴይ፤ እናት ልጅ በጥሩ ሁኔታ ላይ የሚገኙ መሆናቸውን አስታውቀዋል።

