በኦሪጎን 18ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና የተወዳደሩት ኢትዮጵያውያን አትሌቶች በረጅም ርቀት ውድድሮች አዲስ ሬኮርድ ጭምር በማስመዘገብ የሜዳል ባለቤቶች ለመሆን በቅዋል።
ከሰዓታት በፊት በተካሔደው የሴቶች ማራቶን ውድድር የ27 ዓመቷ አትሌት ጎትይቶም ገብረስላሴ ውድድሩን 2 ሰዓት 18 ደቂቃ ከ 11 ሰከንድ በሆነ ውጤት በአንደኛ ደረጃ ጨርሳ የወርቅ ባለቤት ሆናለች።

ጎትይቶም ቀደም ሲል በቶኪዮ 2022 የማራቶን ውድድር 2 ሰዓት 18 ደቂቃ ከ 18 ሰከንድ በመጨረስ ሶስተኛ ሆና የነሐስ ሜዳል ያገኘች ሲሆን፤ በ2021 በጀርመን በተካሔደው የበርሊን ማራቶን 2 ሰዓት 20 ደቂቃ ከ 09 ሰከንድ በማጠናቀቅ ለወርቅ ሜዳል በቅታለች።

ቀደም ባለው ቀንም በኦሪጎን 22 የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮን በተካሔደው የወንዶች ማራቶን የ30 ዓመቱ አትሌት ታምራት ቶላ የሻምፒዮኑን አዲስ ሬኮርድ በማስመዝገብ 2 ሰዓት 5 ደቂቃ ከ 36 ሰከንድ በማጠናቀቅ የወርቅ ሜዳል ባለቤት ሆኗል።

ኢትዮጵያዊው ሞሲነት ገረመው ከታምራት 68 ሰከንዶች ተከትሎ ለብር ሜዳል በቅቷል።

