የኒው ሳውዝ ዌይልስ ፕሪሚየር ዶሚኒክ ፔሮቴይ የነባር ዜጎች ሰንደቅ ዓላማ በቋሚነት እንዲውለበለብ በ2022-23 ክፍለ አገራዊ በጀት የተበጀተለት መሆኑን ገለጡ።
ባንዲራውን በዚህ ዓመት መጨረሻ በሲድኒ የወደብ ድልድይ ላይ በቋሚነት ለማውለብለብ እንዲያስችል ለሰንደቅ ማቆሚያ የሚውል 25 ሚሊየን ዶላር ተመድቧል።
ይህም ማለት የነባር ዜጎች ሰንደቅ ዓላማ በቋሚነት ከአውስትራሊያ ሰንደቅ ዓላማ ጋር ጎን ለጎን በሲዲኒ የወደብ ድልድይ ላይ የሚውለበለብ ይሆናል።
አቶ ፔሮቴይ የወጪው 25 ሚሊየን መሆን ያስደነገጣቸው መሆኑን ጠቅሰው ሆኖም "ለአገራዊ አንድነት የሚከፈል ትንሽ ዋጋ ነው" ብለዋል
የሰንደቁ ርዝመት 20 ሜትር ወይም የስድስት ፎቅ ከፍታ ያለው ሲሆን፤ ሁሉንም የአየር ንብረት መፈራረቆች የሚቋቋም ይሆናል።
የስደተኞች ቀን
የማኅበረሰባት ተወካዮች ከነገ ሰኞ ጁን 20 / ሰኔ 13 ለአንድ ሳምንት ታስቦ የሚከርመውን የስደተኞች ቀን አስመልክተው የፌዴራል መንግሥቱ እስካሁን በጊዜያዊ ቪዛ ላሉ በሺህዎች ለሚቆጠሩ ስደተኞች ቋሚ ዕልባት እንዲያበጅላቸው ጠይቋል።
የአውስትራሊያ ስደተኞች ምክር ቤት ዋና ሥራ አስፈፃሚ ፖል ፓወር አዲሱ የሌበር መንግሥት በጊዜያዊ ቪዛ ላሉ ስደተኞች ቋሚ የመኖሪያ ፈቃድ ለመስጠት የገባውን ቃል በአስቸኳይ ግብር ላይ እንዲያውል ጠይቀዋል።
አቶ ፖል በአሁኑ ወቅት አውስትራሊያ ውስጥ በጀልባ የመጡትን ጨምሮ 19 ሺህ ስደተኞች እንዲሁም 1 ሺህ 100 ከፓፑዋ ኒው ጊኒ እና ናሩ ዕገታ ማዕከላት ተላልፈው የመጡ በጊዜያዊ ቪዛ ፕሮግራም ስር እንደሚገኙ አመላክተዋል።
አዲሱ የሌበር መንግሥት በበኩሉ የምርጫ ዘመቻ ቃሉን ግብር ላይ እንደሚያውል የጠቆመ ቢሆንም ግብር የሚያውልበትን ጊዜ ግና አልገለጠም።

