የአውሮፓ ሕብረትና እንግሊዝ አንግ ሳን ሱ ቺን በመፈንቅለ መንግሥት አስወግዶ ስልጣን የጨበጠውን የምያንማር ወታደራዊ መንግሥት በመቃወም የሁለት ሕይወቶች ማለፍን ተከትሎ ተጨማሪ ማዕቀብ ለመጣል እያሰቡ ነው።
የተቃውሞው መጠን እየበረታ የመጣ ሲሆን፤ የሰሞኑን የማንዳላይ ተቃውሞ ሰልፍ ለመበተን ፖሊስ እውነተኛ ጥይቶችን መተኮሱን የዓይን ምስክሮች ተናግረዋል።
እስካሁን ዩናይድ ስቴትስ፣ እንግሊዝ፣ ካናዳና ኒውዝላንድ ወታደራዊ መሪዎቹ ላይ ያነጣጠሩ ማዕቀቦችን ጥለዋል።
ባለፈው ሳምንት ምያንማር መዲና ናይፒይዳው ጭንቅላቷ ላይ በጥይት ተመትታ ለሞት የበቃችውን የ20 ዓመት ወጣት የተቃውሞ ሰልፈኛ ምያ ትዊት ትዊት ካይንን አክሎ የሟቾች ቁጥር ሶስት ደርሷል።

ጥበበ የማነ ብርሃን
ሎሬየት ዶ/ር ጥበበ የማነ ብርሃን የካቲት 13 ከዚህ ዓለም በሞት ተለይተዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድም ዜና ዕረፍቱን አስመክተው የተሰማቸውን ኃዘን ሲገልጡ "በሕክምና ሞያ፣ በሀገር ሽማግሌነት፣ በርዳታ አስተባባሪነት እና በዕርቀ ሰላም ኮሚሽን አባልነት ሀገራቸውን ያገለገሉት የዓለም ሎሬት ዶር ጥበበ የማነ ብርሃን ማረፋቸውን በመስማቴ የተሰማኝን ኃዘን እገልጣለሁ። ለቤተሰቦቻቸው፣ ለወዳጆቻቸውና ለኢትዮጵያውያን ሁሉ መጽናናትን እመኛለሁ" ብለዋል።

ዶ/ር ጥበበ በሙያቸው ዘርፍ በዓለም አቀፍ የምርምር ማዕከላትና የማሰልጠኛ መካነ ተቋማት በተመራማሪ ስይንቲስቲነትና የሕዝብ ጤና ሥራ አስኪያጅነት ከአንድ አሠርት ዓመት በላይ አገልግለዋል። ከ65 በላይ ሳይንሳዊ ጥናቶቻቸውም በዓለም የጥራት ደረጃቸው የላቀ ጆርናሎች ላይ ለሕትመት በቅተዋል።
ዶ/ር ጥበበ ሐሩራዊ በሽታዎችን በ2020 በቁጥጥር ስር አውሎ መክላት እንዲቻል ግፊት ሲያደርጉ ነበር።
ሱዳንና ግብፅም ከኢትዮጵያ ጋር ያላቸውን ልዩነቶች በሰላማዊ መንገድ እንዲፈቱ ዲፕሎማሲያዊ ጥረቶችን አበርክተዋል።
በሙያቸው ዘርፍ ላበረከቷቸው ዓለም አቀፍ አስተዋፅዖዎቻቸውም ከአሜሪካ ግለታሪካዊ መካነ ተቋም ያገኙትን የዓለም ሎሬየት አክሎ በርካታ የክብር ሽልማቶችን ያገኙ ሲሆን ከራሺያው ፕሬዚደንት ቭላድሚር ፑቲንም የፑሽኪን ሜዳል ተሸልመዋል።
ዶ/ር ጥበበ በሕይወት ሳሉ ጎልፍ መጫወት፣ ረቂቅ ሙዚቃ ማድመጥና መጽሐፍትን ማንበብ ይወዱ ነበር። ከባለቤታቸው ዶ/ር ያለም አምባየም ሁለት ሴት ልጆችን አፍርተዋል። ሁለት የልጅ ልጆችም አሏቸው።
ቴኒስ አውስትራሊያ
በሴቶች ዓለም አቀፍ የሜዳ ቴኒስ አሸብራቂ ኮከብ እየሆነችው የመጣችው ናኦሚ ኦሳካ የዘንድሮው የአውስትራሊያ ኦፕን 2021 ቴኒስ አሸናፊ ሆናለች።
ናኦሚ ትናንት ፌብሪዋሪ 20 ሜልበርን በተካሔደው የመጨረሻ የአውስትራሊያ ኦፕን ለአሸናፊት የበቃችው አሜሪካዊቷን ጄኔፈር ብራዲን 6-4 6-3 በመርታት ነው።

ገና የ23 ዓመት ወጣትና የአራት ግራንድ ስላም አሸናፊ የሆነችው ናኦሚ ከዊሊያምስ እህትማማቾችና ኪም ክላስተር በስተቀር በርካታ ግጥሚያዎች በማሸነፍ ከሌሎች ሴት ቴኒስ ተጫዋቾች የላቁ ድሎችን በማህደሯ አስፍራለች።

